Fana: At a Speed of Life!

ለሚ ኩራ የአዲስ አበባ 11ኛው ክፍለ ከተማ ሆኖ መዋቀሩ የአገልግሎት አሰጣጡን ተደራሽ፣ ፍትሃዊ እና ቀልጣፋ እንደሚያደርገው ነዋሪዎች ገለፁ

አዲስ አበባ ፣ጥቅምት 14 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ)የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቅርቡ አስራ አንደኛ ክፍለ ከተማ በአዲስ እንዲዋቀር የወሰነው ውሳኔ በአካባቢው የሚኖሩ አርሶ አደሮችን ጥያቄ የመለሰ መሆኑን ነዋሪዎች ገለጹ።

ለሚ ኩራ የአዲስ አበባ 11ኛው ክፍለ ከተማ ሆኖ መዋቀሩ የአገልግሎት አሰጣጡን ተደራሽ፣ ፍትሃዊ እና ቀልጣፋ እንዲሆን ያስችላል ያሉት የአካባቢው ነዋሪዎች ለከተማ አስተዳደሩ ምስጋና አቀርበዋል፡፡

በየካ እና በቦሌ ክፍለ ከተሞች ስር በመሆን ይተዳደሩ የነበሩት የሰሚት፣ የመሪ፣ የአያት፣ የየካ አባዶ፣ ጎሮ፣ አይሲቲ ፖርክ እና አካባቢው ነዋሪዎች በአያት አደባባይ በመገኘት ደስታቸውን ገልፀዋል፡፡

ነዋሪዎቹ ክፍለ ከተማው በአቅርቢያችን መዋቀሩ አስተዳደራዊ አገልግሎቶችን በቅርበት ለማግኘት፣ እንግልትን ለመቀነስ፤ ልማትን ለማፋጠን እና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት ሁለንተናዊ ፋይዳ አለው ብለዋል።

የለውጡ አመራር ለዘመናት ለቆየው የህዝብ ጥያቄ አፋጣኝ መልስ በመስጠቱ መደሰታቸውንም ገልጸዋል፡፡

በምስጋና መርሃ-ግብሩ ላይ የየካ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ተክሌ እና የቦሌ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መኮንን አምባዬ እንዲሁም የአዲሱ ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ኤልያስ መሀመድ በእንግድነት ተጋብዘው ለአካባቢው ነዋሪዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ከአዲስ አበባ ከተማ ፕሬስ ሴክሬታሪ ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.