Fana: At a Speed of Life!

በመጀመሪያው ሩብ ዓመት በወጪ ንግድ ዘርፍ ከታሰበው 95 በመቶው ተሳክቷል

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 13፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በተያዘው በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት በወጪ ንግድ ዘርፍ ከታሰበው 95 በመቶውን ማሳካት መቻሉን ንግድ እና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የ10 ዓመት መሪ ልማት እቅድ ዝግጅት ምዕራፍ እና የ2013 ዓ.ም እቅድ አፈፃፀምን ከክልል ከተማ አስተዳደር ንግድ እና ኢንዱስትሪ አካላት እንዲሁም ከተጠሪ አካላት ጋር እየገመገመ ይገኛል፡፡
በዚህም ሚኒስቴሩ በንግድ ዘርፍ የፖሊሲ ማሻሻያ እና አሰራር ሪፎርም በሚያስፈልጋቸው ተቋማት ላይ ሰፊ ስራዎች በመስራት አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ገልጿል፡፡
በወጪ ንግዱም በሩብ ዓመቱ 95 በመቶ ያሳካ ሲሆን 839 ሚሊየን ብር የውጭ ምንዛሬ ማግኘቱንም አስታውቋል፡፡
ከዚህ ውስጥ የግብርናው ዘርፍ 541 ሚሊየን ብር ወይም 73 በመቶ አፈፃፀም በማሳየት ቀዳሚው ነው ተብሏል፡፡
የማምረቻው ዘርፍም 94 ሚሊየን ዶላር ያስገኘ ሲሆን የእቅዱን 95 በመቶ አሳክቷልም ነው የተባለው፤ የውጭ ምንዛሬ ድርሻውም 11 በመቶ ደርሷል፡፡
የማዕድን ዘርፉ ከ205 ሚሊየን ዶላር በላይ በሆነ ገቢ 24 በመቶ የውጭ ምንዛሬ አስገኝቷል ነው የተባለው፡፡
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አምራች ዘርፉን ለማሳደግ ሰፊ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ገልፆ ለአብነትም ከአምስት ወራት በፊት ከፍተኛ የምርት እጥረት የታየበትን የሲሚንቶ ምርት ማሻሻሉን ገልጿል፡፡
በዚህም በቀን 102 ሺህ ኩንታል ሲሚንቶ ሲመረት የነበረውን አሁን ላይ በተደረገው ድጋፍ በቀን 310 ሺህ ኩንታል ሲሚንቶ ማምረት መቻሉን አስታውቋል፡፡
በመድረኩ የንግድ እና ኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበልን ጨምሮ ሌሎች የተጠሪ ተቋምት ሃላፊዎች እና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡
በፍሬህይወት ሰፊው
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.