Fana: At a Speed of Life!

በምርጫ ወቅት ሊኖር በሚገባው የኮቪድ 19 ጥንቃቄ ዙሪያ ምክክር ተካሄደ

አዲስ አበባ ፣ ጥቅምት 20 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በምርጫ ወቅት ሊኖር በሚገባው የኮቪድ 19 ጥንቃቄ ዙሪያ ያተኮረ ምክክር ተካሄደ፡፡

የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ባዘጋጀው ምክክር መድረክ ላይ የሲቪል ማህበራት እና የመገናኛ ብዙሃን ተሳትፈዋል።

የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ለምርጫው የጥንቃቄ እርምጃ ማስፈጸሚያ የሚሆን 1 ነጥብ 1 ቢሊየን ብር እንደሚያስፈልግ ጠቅሶ ተጨማሪ የገንዘብ ድጋፍ ጠይቋል።

በተለይም በምርጫ ወቅት አስፈላጊውን ጥንቃቄ እያደረጉ ምርጫን ለማካሄድ ተጨማሪ የሰው ሃይል እና ተጨማሪ በጀት ያስፈልጋል ተብሏል።

ከምርጫ አስፈጻሚዎች በተጨማሪ አካላዊ ርቀርን የሚያስጠብቁ ሰዎች በየምርጫ ጣቢያዎች ያስፈልጋሉም ነው የተባለው፡፡

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በወሰነው መሰረት ስድስተኛው ሃገራዊ ምርጫ በያዝነው አመት መካሄድ ስላለበት ቦርዱ መደረግ ባለባቸው ጥንቃቄዎች እና የድርጊት መርሃ ግብሮችን መነሻ ሃሳብ አቅርቧል።

በዚህም ምርጫውን በግንቦት የመጨረሻዎቹ ሁለት ሳምንታት አልያም በሰኔ ወር የመጀመሪያ ሁለት ሳምንታት ለማካሄድ የመነሻ ሃሳብ ቀርቧል።

በዚህም መነሻ ከታህሳስ እስከ ጥር አጋማሽ ድረስ የምርጫ አስፈጻሚዎችን ስልጠና ለመስጠት እንደመነሻ ተቀምጧል።

ከጥር አጋማሽ እስከ የካቲት ሶስተኛ ሳምንት ደግሞ የመራጮችን ምዝገባ ለማካሄድ መታቀዱም ተጠቅሷል።

ከየካቲት መጀመሪያ እስከ የካቲት አጋማሽ የእጩዎች ምዝገባ እንዲሁም ከየካቲት አጋማሽ እስከ ምርጫው ማካሄጃ ሳምንት ድረስ ደግሞ የምርጫ ቅስቀሳ ይካሄዳል በሚል ተቀምጧል።

ከምርጫው ጋር ተያይዞ የኮቪድ 19 ጥንቃቄን የሚከታተል ግብረ ሃይል እንደሚቋቋምም ነው የተገለጸው።

ለምርጫው ስኬታማነት የጤና ሚኒስቴር፣ የገንዘብ ሚኒስቴር፣ የፀጥታ አካላትን ጨምሮ ሌሎች ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን እንዲወጡ የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ጠይቀዋል።

በምስክር ስናፍቅ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.