Fana: At a Speed of Life!

በቆላ አካባቢዎች እና አርብቶአደር ዜጎች የልማት ጉዞ ላይ ያተኮረው አዲስ ወግ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው

አዲስ አበባ፣ ጥር 6፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ ወግ፤ አንድ ጉዳይ ውይይት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አዘጋጅነት እየተካሄደ ነው፡፡

የዛሬው የውይይት መድረክ በቆላ አካባቢዎች እና አርብቶአደር ዜጎች የልማት ጉዞ ላይ ያተኮረ ነው፡፡

በውይይቱ ላይ የመነሻ ፅሁፍ የቀረበ ሲሆን ወይዘሮ ሃኒ ሁሴን የአርብቶ አደርና የስነ ጾታ ባለሙያ ባቀረቡት የመነሻ ፅሁፍ አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ በትክክል ያለመረዳት ችግር መኖሩን ጠቅሰዋል፡፡

አርብቶ አደሩ ያለውን ውስን ሃብት በስትራቴጂ የሚጠቀም እንጅ እንዲሁ ዝም ብሎ ከቦታ ቦታ የሚሽከረከር አይደለምም ብለዋል፡፡

የውሃ፣ የመኖ እና ሌሎች አስፈላጊ ነገሮች በአንድ ቦታ ባለመገኘታቸው አርብቶ አደሩ በአንድ ቦታ ላይ ረግቶ እንዳይቀመጥ ያደረጉት ምክንያቶች መሆናቸውንም አስረድተዋል፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን አርብቶ አደር በሙሉ አንድ አድርጎ የማየት ችግር እንዳለ ጠቅሰው፥ በዚህ ምክንያት በሃገሪቱ ውስጥ በሚተገበሩ ፖሊሲዎች አርብቶ አደሩ ተጠቃሚ ሳይሆን ቆይቷልም ነው ያሉት፡፡

አቶ አብዱራህማን አዲ ጣሂር የሶማሌ ክልል መስኖና ተፋሰስ ቢሮ ሃላፊ በበኩላቸው በኢትዮጵያ የአርብቶ አደር ልማት ሁልጊዜ ከፀጥታ ጋር ብቻ ተያይዞ መተግበሩ ውጤታማ እንዳይሆን እንዳደረገው አንስተዋል፡፡

ባለፉት አመታት የተከናወነው የመንደር ማሰባሰብ ስራ ከሪፖርት የተሻገረ እንዳለሆነም አስታውሰዋል፡፡

አርብቶ አደሩ ለኢትዮጵያ ጠቅላላ የሃገር ውስጥ ምርት እድገት እስከ 15 በመቶ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ሲሆን፥ ኢትዮጵያ በምትልካቸው የቁም እንስሳት የስጋ ምርቶች ደግሞ ከ95 በመቶ በላይ እንደሚያበረክትም ገልጸዋል፡፡

ይሁን እንጅ ተገቢ ትኩረት እንዳልተሰጠው አስታውቀዋል፡፡

በአንጻሩ በትምህርት እና በእንስሳት ጤና ጥሩ ውጤት መገኘቱን ነው የገለጹት፡፡

የግብርና ሚኒስር ዲኤታው ዶክተር ማንደፍሮ ታደሰ መንግስት አሳታፊ፣ አካታች እና ዘላቂነት ያለው ልማት በአርብቶ አደሩ አካባቢ ለማምጣት የፖሊሲ ለውጥ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡

ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግ ልማት ይተገበራልም ነው ያሉት፡፡

የአርብቶ አደር አካባቢ በኢትዮጵያ 60 በመቶ የቆዳ ስፋት እንዲሁም እስከ 14 በመቶ የህዝብ ብዛት ቁጥርን ይሸፍናል ተብሏል፡፡

አርብቶ አደር በስድስት ክልሎች ማለትም አፋር፣ ሶማሌ፣ ኦሮሚያ፣ ጋምቤላ፣ ደቡብ እና ቤኒሻንጉል ክልሎች ይኖራል፡፡

በአላዛር ታደለ

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.