Fana: At a Speed of Life!

በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ሁለት ወራት 42 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ገቢ ተሰበሰበ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 8፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ)በ2013 በጀት አመት የመጀመሪያዎቹ ሁለት ወራት 42 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

የሚኒስቴሩ የስራ ኃላፊዎች የ2013 በጀት አመት የገቢ አሰባሰብ እቅድ እና በበጀት ዓመቱ የሁለት ወራት አፈፃፀም ዙሪያ ውይይት አካሂደዋል፡፡

በዉይይቱ ወቅት እንደተገለፀው በሀምሌና በነሀሴ ወር 39 ቢሊየን 430 ሚሊየን 954ሺህ 692 ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ 42 ቢሊየን 204 ሚሊየን 26 ሺህ ብር በመሰብሰብ የእቅዱን 107 በመቶ በላይ ማሳካት ተችሏል፡፡

ይህም ከባለፈው ተመሳሳይ ሁለት ወር ጋር ሲነጻጸር የ10 ነጥብ 7 በመቶ ብልጫ አለው፡፡

በ2013 በጀት አመት ከሀገር ውስጥ ታክስ ብቻ 164 ነጥብ 29 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ የታቀደ ሲሆን ይህም በ2012 ከሀገር ውስጥ ታክስ ከተሰበሰበው 128 ነጥብ 67 ቢሊየን አንጻር የ35 ነጥብ 62 ቢሊየን ብር ብልጫ እንዳለው ነው የተገለጸው፡፡

እቅዱን ለማሳካት የሚያስችል የተረጋጋ እና ጥሩ አቅም ያለው ሰራተኛ መኖሩና በሰራተኛውና በአመራሩ መካከል ያለው ተቀራርቦ መስራት ከምንጊዜውም በላይ እያደገ በመሆኑና ግብር ከፋዮች ግብራቸውን በፈቃደኝነት የመክፈል ባህል እዳበረ በመምጣቱ ለዕቅዱ መሳካት አስተዋፅኦ አበርክቷል ነው የተባለው፡፡

በውይይቱ ላይ የተገኙት የገቢዎች ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው ያቀድነውን ብቻ ሳይሆን ከዚያም በላይ ለመሰብሰብ መስራት አለብን ማለታቸውን ከገቢዎች ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.