Fana: At a Speed of Life!

በትግራይ ክልል ተቋርጦ የነበረው የአሮጌ ብር ኖት ቅያሬ ድጋሚ ተጀምሯል

አዲስ አበባ ፣ ታህሳስ 21 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በትግራይ ክልል ተቋርጦ የነበረው የአሮጌ ብር ኖት ቅያሬ ድጋሚ ተጀምሯል፡፡

የብር ቅያሬው ቅዳሜና እሁድን ጨምሮ ከዛሬ ታህሳስ 21 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በ14 ቀናት ውስጥ እንደሚከናወን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ለጣቢያችን በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

ባንኩ በመግለጫው መንግስት በክልሉ በወሰደው የህግ ማስከበር ዘመቻ ምክንያት የአሮጌ ብር ኖት ቅያሬው ተቋርጦ እንደነበር አስታውሶ አሁን ላይ በተወሰኑ የክልሉ ከተሞች የመብራትና የኢንተርኔት አገልግሎት በመጀመሩ በእነዚሁ አካባቢዎች ባንኮች ሥራ እንዲጀምሩ እየተደረገ ይገኛል ብሏል፡፡

በዚህ መሰረት ተቋርጦ የነበረውን የአሮጌ ብር ኖት ቅያሬ ማስቀጠል አስፈላጊ በመሆኑ ባንኮች ሥራ ከጀመሩበት ቀን ጀምሮ ቅዳሜና እሁድን ጨምሮ በ14 ቀናት ውስጥ አሮጌ ብር እንዲቀይሩ ከዛሬ ታህሳስ 21 ቀን 2ዐ13 ዓ.ም. ጀምሮ ተወስኗልም ነው ያለው፡፡

ባንኮችም ይህንኑ ተከታትለው እንዲያስፈጽሙ እና ተግባራዊ እንዲያደርጉ በመጠቆም በብር መቀየሩ ሂደት የነበሩ መመሪያዎችና አሠራሮች እንደተጠበቁ መሆናቸውንም ገልጿል፡፡

ከባንክ በጥሬ ገንዘብ የሚወጣው የገንዘብ መጠን ላይ በተሻሻለው መመሪያ ላይ በተቀመጠው መሠረት ተፈፃሚ ይሆናልም ብሏል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞም ከ1ዐዐ ሺህ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን አሮጌ ብር ያላቸው የመቀየሪያው የጊዜ ገደብ የህግ ማስከበሩ ከመጀመሩ በፊት የተጠናቀቀ በመሆኑ ብር መቀየር የሚችሉት ከ1ዐዐ ሺህ ብር በታች ያላቸው መሆናቸውንም አስታውቋል፡፡

ባንኮችም ይህንኑ ሥራ የሚከታተል ግብረ ኃይል በማቋቋም መመሪያን በጠበቀ መልኩ እንዲሠሩ እና በእያንዳንዱ የባንክ ቅርንጫፍ የብር መቀየር ሥራ የተጀመረበትንና የተጠናቀቀበት ቀን እና የተለወጠ የብር መጠን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በየሳምንቱ ሪፖርት እንዲያደርጉም አሳስቧል፡፡

ከመስከረም 6 ቀን 2ዐ13 ዓ.ም. ጀምሮ ለሶስት ወራት በመላ ሀገሪቱ አሮጌ ብር በአዲስ ብር የመቀየር ሥራ ሲሰራ መቆየቱ ይታወሳል፡፡

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.