Fana: At a Speed of Life!

በኢትዮጵያ በአንድ ቀን ብቻ 100 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ተገኘባቸው

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 20፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ በተደረገው 4 ሺህ 950 የላብራቶሪ ምርመራ 100 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ እንደተገኘባቸው የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 831 መድረሱን የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ በዛሬው እለት ባወጡት ሪፖርት ገልፀዋል።

ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች መካከል 99 ኢትዮጵያውያን እና አንድ የቡሪንዲ ዜጋ ሲሆኑ እድሜያቸው ከ3 እስከ 70 ዓመት የሆኑ 53 ወንዶችና 47 ሴቶች ናቸው።

ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል 62 ሰዎች የውጭ ሀገር የጉዞ ታሪክ እና በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት የሌላቸው፣ 3 ሰዎች የውጭ የጉዞ ታሪክ ያላቸው እንምዲሁም 35 ሰዎች በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት ያላቸው መሆኑን አስታውቀዋል።

ቫይረሱ በምርመራ ከተገኘባቸው ሰዎች ውስጥ 94 ሰዎች ከአዲስ አበባ ሲሆኑ፥ ከእነዚህም መካከል 60 ሰዎች የውጭ ሀገር የጉዞ ታሪክ እና በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት የሌላቸው፣ 34 ሰዎች በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር ግንኙነት ያላቸው ናቸው።

1 ሰው ከትግራይ ክልል (የውጭ ሀገር የጉዞ ታሪክ ያለውና በለይቶ ማቆያ የሚገኝ)፣ 2 ሰዎች ሶማሌ ክልል (ሁሉም የውጭ ሀገር የጉዞ ታሪክ ያላቸውና በለይቶ ማቆያ የሚገኙ)፣ 3 ሰዎች ኦሮሚያ ክልል ( 2 ሰዎች የውጭ ሀገር የጉዞ ታሪክ እና በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት የሌላቸው፣ 1 ሰው በበሽታው ከተያዘ ሰው ጋር የታወቀ ግንኙነት ያለው መሆናቸውን ዶክተር ሊያ ገልፀዋል።

በተጓዳኝ ህመም ምክንያት ህክምና ላይ የነበሩ የ70 ዓመት እድሜ ያላቸው ሴት ለኮሮና ቫይረስ በተደረገ ምርመራ ናሙና ከተወሰደ በኋላ የምርመራ ውጤት ሳይደርስ ህይወታቸው አልፏል፤ በምርመራው ውጤትም ቫይረሱ እንዳለባቸው ስለተረጋገጠ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 7 ደርሷል።

የጤና ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በህልፈተ ህይወታቸው የተሰማቸውን ሀዘን በመግለፅ፤ ለቤተሰቦቻቸው መፅናናትን ተመኝተዋል።

በሌላ መልኩ በትላንትናው ዕለት 10 ሰዎች ከአዲስ አበባ ከበሽታው ያገገሙ ሲሆን፥ በአጠቃላይ ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 191 ደርሷል።

በ 24 ሰዓታት ውስጥ የተደረጉ የላቦራቶሪ ምርመራ ናሙናዎቹ ከተለያዩ ይበልጥ ተጋላጭ ከሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ከጤና ተቋማት፣ በቫይረሱ ከተያዘ ሰው ጋር የቅርብ ንክኪ ካላቸው ሰዎች እንዲሁም በአስገዳጅ ለይቶ ማቆያ ውስጥ ካሉ ሰዎች ተወስዶ የተከናወነ መሆኑንም አስታውቀዋል።

ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ እስካሁን ለ96 ሺህ 566 ሰዎች ምርመራ የተደረገ ሲሆን፥ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 831 ደርሷል።

አሁን ላይ 631 ሰዎች በህክምና ላይ ሲሆኑ፥ እስካሁንም 191 ሰዎች ከቫይረሱ አገግመዋል፤ የሰባት ሰዎች ህይወት ሲያልፍ፤ 2 ሰዎች ወደ ሀገራቸው ጃፓን መመለሳቸው ይታወሳል።

#FBC

የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.