Fana: At a Speed of Life!

በዓለም ላይ በኮሮና ቫይረስ የተያዙ ሰዎች 37 ሚሊየን አለፈ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 30፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በዓለም ዓቀፍ ደረጃ በኮሮና ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 37 ሚሊየን አለፈ።

ዎርልዶሜትር በበይነመረቡ ይፋ እንዳደረገው በወረርሽኙ አማካኝነት ከ1 ሚሊየን 73 ሺህ በላይ ሰዎች ለህልፈት መዳረጋቸውን ነው ያሰፈረው፡፡

በተጨማሪም 28 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች ከኮሮና ቫይረስ ማገገማቸውንም ነው የገለጸው፡፡

ቫይረሱ አሁንም እየተሰራጨባቸው ካሉ አገራት መካከል አሜሪካ፣ ህንድ፣ ብራዚል፣ ሩስያ እና ኮሎምብያ ዋነኞቹ ናቸው ተብሏል፡፡

አሜሪካ ወደ 8 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች ቫይረሱ የተገኘባቸው ሲሆን 218 ሺህ 685 ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡

በህንድ በቫይረሱ ከተያዙ 7 ሚሊየን ከሚጠጉ ሰዎች ውስጥ ከ107 ሺህ በላይ ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡

በብራዚል ከ5 ሚሊየን በላይ ሰዎች የተያዙ ሲሆን የሟቾቹ ቁጥር ከአሜሪካ ቀጥሎ 149 ሺህ 692 ደርሷል፡፡

በአፍሪካ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች 1 ሚለየን 557 ሺህ 465 መድረሱን የዓለም ጤና ድርጅት አስታውቋል፡፡

በቫይረሱ ከተያዙት ውስጥ ከ1 ሚሊየን 214 በላይ ሰዎች ሲያገግሙ 37 ሺህ 620 ሰዎች ለህልፈት ተዳርገዋል፡፡

በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የኮሮና ቫይረስን ተከትሎ የተጣሉ እገዳዎች መነሳታቸውን ተከትሎ ወረርሽኙ ዳግም እየተስፋፋ ይገኛል ተብሏል፡፡

በዚህም ከ1 ሚሊየን 285 ሺህ በላይ ዜጎቿ በቫይረሱ የተያዙባት ሩስያ በአንድ ቀን ብቻ 12 ሺህ 846 ሰዎች በቫይረሱ ተይዘውባታል፡፡

ይህም ኮሮና ቫይረስ አገሪቱ ከገባ በኋላ በአንድ ቀን የተመዘገበ ትልቁ ቁጥር ነው ተብሏል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.