Fana: At a Speed of Life!

በጅማ ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል እየተተገበረ ያለው የተቀናጀ የአንቡላንስ አገልግሎት ተሞክሮ ሊስፋፋ ይገባል ተባለ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 24፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በጅማ ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል እየተተገበረ ያለው የተቀናጀ የአንቡላንስ አገልግሎት ወደሌሎች አካባቢዎች ሊስፋፋ ይገባል ተባለ።

በአምስት የሀገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች እየተተገበረ ያለው የድንገተኛ አደጋዎች እና የጽኑ ህሙማን ህክምና አስመልክቶ የሚመክር አውደ ጥናት በጤና ሚኒስቴር እና በጅማ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት በጅማ ከተማ ተካሂዷል።

የጤና ሚኒስትር ዲኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ የጤና ሚኒስቴር የድንገተኛ እና ጽኑ ህሙማን ህክምናን ተደራሽ ለማድረግና አሰራሩን ለማሻሻል ስልት ተነድፎ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።

በዚሁ መሰረት የጅማ ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል የተቀናጀ የአንቡላንስ አገልግሎትን በአንድ ማዕከል በመስጠት ረገድ እያከናወነ ያለው ተግባር ወደ ሌሎች አካባቢዎች ሊስፋፋ የሚገባው ምርጥ ተሞክሮ እንደሆነም ነው የተናገሩት።

የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ጀማል አባፊጣ በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው የህብረተሰብ አገልግሎት በማስፋፋት እና ችግር ፈቺ የሆኑ የምርምር ስራዎችን በማቅረብ ረገድ ልምድ ያለው መሆኑን አስታውሰዋል።

በጤናው ዘርፍም ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ለጅማ ከተማ እና ለአካባቢው ማህበረሰብ የጤና ግልጋሎት እየሰጠ ሲሆን በቴክኖሎጂ ተደግፎ እየተሰጠ ያለው የተቀናጀ የአንቡላንስ አገልግሎት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።

በቀጣይም ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር አገልግሎቱ እንዲስፋፋ እና እንዲዘምን ዩኒቨርሲቲው ይሰራል ብለዋል።

በአውደ ጥናቱ የተቀናጀ የአንቡላንስ አገልግሎት ከሚተገበርባቸው ከተሞች በመጡ የዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል ምሁራን የድንገተኛ እና ጽኑ ህክምና አገልግሎቶችን አስመልክቶ ሪፖርቶች የቀረቡ ሲሆን የከተማዎቹ ከንቲባዎችና ተወካዮች በተገኙበት ምክክር ተደርጓል።

ሚኒስትር ዲኤታው እና የአውደ ጥናቱ ተሳታፊዎችም በጅማ ዩኒቨርሲቲ እና በአጋሮ የሚገኙ ሆስፒታሎችን መጎብኘታቸውን ከሚኒስቴሩ ለመረዳት ችለናል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.