Fana: At a Speed of Life!

በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ ልምድ ለመለዋወጥ እና በትብብር ለመስራት ከደቡብ ሱዳን ልዑካን ጋር ውይይት ተደረገ

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 12 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የገቢዎች ሚኒስቴር በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ ልምድ ለመለዋወጥ እና በትብብር ለመስራት ከደቡብ ሱዳን የሃገር ውስጥ ታክስና ጉምሩክ ልዑካን ጋር ተወያየ፡፡

በገቢዎች ሚኒስቴር የህግ ተገዥነት ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ዘመዴ ተፈራ ኢትዮጵያና ሱዳን ድንበር ብቻ የሚጋሩ ሳይሆን የጋራ ህዝብ ያላቸውና ባህል የሚጋሩ መሆናቸውን ጠቁመው ለሁለቱ ሀገራት ህዝብ ተጠቃሚነት እና ብልፅግና በጋራ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

በውይይቱ ወቅት የኢትዮጵያን የገቢ አሰባሰብ ልምድ በተመለከተ ለልዑካን ቡድኑ ገለፃ ተደርጓል፡፡

ከነዳጅ ውጭ ባሉ የግብር አሰባሰብ እና ዓለም አቀፍ የጉምሩክ ስነ-ስርዓትን በተመለከተ ደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያን ልምድ መውሰድ እንደምትፈልግ የሀገሪቱ የገቢዎች ባለስልጣን የስራ ኃላፊዎች ገልፀዋል፡፡

በኢትዮጵያ የደቡብ ሱዳን አምባሳደር ጀምስ ፒታ ሞርጋን በበኩላቸው ኢትዮጵያን እንደ ቤታቸው እንደሚቆጥሯትና በሀገራቸው ያለመረጋጋት በነበረበት ወቅት ኢትዮጵያ ተቀብላ እንደ ዜጓቿ እንዳስተናገደቻቸው አስረድተዋል፡፡

በድንበር አካባቢ የሚደረግ ንግድ በአግባቡ በማስተዳደር ሁለቱ ሃገራት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የጉምሩክ ኬላዎችን ማቋቋም እንደሚገባ በውይይቱ ወቅት ተገልጿል፡፡

በቀጣይ በሀገር ውስጥ ገቢ እና በጉምሩክ ዘርፍ በትብብር ለመስራት የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ለመስራት ከሁለቱ ሃገራት የተውጣጣ የቴክኒክ ባለሙያዎች በዝርዝር ውይይት አድርጎ የመግባቢያ ስምምነት በመፈራረም ወደ ስራ እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.