Fana: At a Speed of Life!

በጉራ ፈርዳ ወረዳ ለሰው ህይወት መጥፋት እና ለንብረት ውድመት ምክንያት ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ 54 ሰዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 17፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) በቤንች ሸኮ ዞን ጉራ ፈርዳ ወረዳ ለሰው ህይወት መጥፋት እና ለንብረት ውድመት ምክንያት ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ 54 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገለጸ፡፡

የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፍቅሬ አማን እንደገለጹት ሰሞኑን በጉራ ፈርዳ ወረዳ ለ31 ሰዎች ሞት ለንብረት ውድመት እና ለአካል ጉዳት መንስኤ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ 54 ሰዎች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡

ከተጠርጣሪዎቹ መካከል ከዞን እስከ ቀበሌ ባለው መዋቅር ያሉ ሰባት አመራሮች እና ሁለት የፖሊስ አባላት እንደሚገኙበት ገልፀዋል፡፡

በዚህም ህብረተሰቡን በማሳተፍ ተጠርጣሪዎችን ወደ ህግ የማቅረብ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል፡፡

በዞኑ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ምክንያት ከ5 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች መፈናቀላቸውን የተናገሩት ዋና አስተዳዳሪው ተፈናቃዮችችን መልሶ ለማቋቋም የአካባቢው ህብረተሰብ ድጋፍ በማድረግ ላይ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡

ለዚህም በተደረገው ጥረት የዞንና የወረዳው መንግስት ከ1 ነጥብ 1 ሚሊየን ብር በላይ በመመደብ አስፈላጊው ሰብዓዊ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ዋና አስተዳዳሪው መናገራቸውን ከደቡብ ክልል መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.