Fana: At a Speed of Life!

በጎንደሩ የፀጥታ መደፍረስ የተሳተፉ አጥፊዎችን መንግስት አጣርቶ እርምጃ እንዲወስድ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጠየቀ

አዲስ አበባ፣ሚያዝያ 20፣2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በጎንደር በተከሰተው የፀጥታ መደፍረስ ላይ እጃቸው ያለበትን አጥፊዎች መንግስት አጣርቶ እርምጃ እንዲወስድ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጠየቀ።
 
ጉዳዩን አስመልክቶ መግለጫ የሰጡት ተቀዳሚ ሙፍቲ ሀጂ ኡመር ኢድሪስ፥ በጎንደር በተከሰተው ግጭት በደረሰው የህይወት መጥፋትና ንብረት ውድመት ማዘናቸውን ገልፀው፥ የፌደራል መንግስትም ሆነ የክልሉ መንግስት በአስቸኳይ አጥፊዎችን ለህግ ማቅረብ እንደሚገባቸው ነው የተናገሩት።
 
ከጊዜ ወደ ጊዜ በአፋቸው ሰላም የሚሰብኩ ነገር ግን በጎን ወንድም ወንድሙን እንዲገድል የሚሰሩ አሉ ያሉት ተቀዳሚ ሙፍቲ ሀጂ ኡመር ኢድሪስ፥ መንግስት በእንዲህ ያለው ላይ ህጋዊ እርምጃ መውሰድ አለበት ብለዋል።
 
ማንኛውም ሃይማኖት ግድያን እንደማያስተምር በመግለፅ፥ የኃይማኖት አባቶችም ህዝቡ ወደ አንድነት እንዲመጣ ማስተማር አለብን ሲሉ ተናግረዋል።
 
በተጨማሪም ህዝበ ክርስቲያኑም ሆነ ህዝበ ሙስሊሙ ተባብሮ አጥፊዎችን ሊታገልና ተግባሩንም ማውገዝ አለበት ነው ያሉት።
 
ንብረታቸው የወደመባቸውንም ሆነ የተጎዳውን የሚያጣራ ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደ ስራ እንደሚገባ የተጠቆመ ሲሆን፥ ለተጉዱትም እርዳታ የሚያሰባስብ ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደስራ ይገባል ተብሏል።
 
በዓለምሰገድ አሳዬ
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.