Fana: At a Speed of Life!

በ24 ሰዓታት ውስጥ 164 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ሲገኝባቸው፤ የ5 ሰዎች ህይወት አለፈ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 4፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ በተደረገው 6 ሺህ 630 የላብራቶሪ ምርመራ 164 ሰዎች የኮሮና ቫይረስ እንደተገኘባቸው የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

በአጠቃላይ በሀገራችን ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 2 ሺህ 670 መድረሱንም የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ አስታውቀዋል።

ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ፥ የእድሜ ክልላቸው ከ1 እስከ 92 ዓመት ውስጥ የሚገኝ 117 ወንዶች እና 47 ሴቶች ናቸው።

ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከልም 104 ሰዎች ከአዲስ አበባ፣ 4 ከትግራይ ክልል፣ 2 ከኦሮሚያ ክልል፣ 22 ከአማራ ክልል፣ 26 ከሶማሌ ክልል፣ 4 ከደቡብ ክልል፣ 1 ከሐረሪ ክልል እንዲሁም 1 ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እንደሆኑም ገልጸዋል።

ከኮሮና ቫይረስ ጋር በተገናኘ የ5 ኢትዮጵያውያን ህይወት ማለፉንም የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ በሪፖርታቸው አስታውቅዋል።

በቫይረሱ ህይወታቸው ካለፈ ሰዎች መካከል የ92 እና የ58 ዓመት እድሜ ያላቸው ሁለት የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በአስክሬን ምርመራ ቫይረሱ የተገኘባቸው መሆኑም በሪፖርቱ አስታውቀዋል።

ቀሪዎቹ የ80 እና የ36 ዓመት የአዲስ አበባ ነዋሪዎችና የ70 ዓመት የሶማሌ ክልል ነዋሪ በህክምና ማዕከል ውስጥ በህክምና ላይ የነበሩ መሆናቸውም ታውቋል።

በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቫይረሱ የተገኘባቸው እና ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 40 መድረሱን አስታውቀዋል።

በሌላ መልኩ በትላንትናው ዕለት 33 ሰዎች (32 ከአዲስ አበባ እና 1 ከአማራ ክልል) ያገገሙ ሲሆን በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ከቫይረሱ ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 434 መሆኑንም ዶክተር ሊያ አስታውቀዋል።

ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ እስካሁን ለ165 ሺህ 151 ሰዎች ምርመራ የተደረገ ሲሆን፥ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 2 ሺህ 670 ደርሷል።

አሁን ላይ 2 ሺህ 194 ሰዎች በህክምና ላይ ሲሆኑ፥ ከእነዚህም ውስጥ 32 ሰዎች በጽኑ የታመሙ መሆናቸውንም የጤና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።

እስካሁን በኢትዮጵያ 434 ሰዎች ከቫይረሱ ሲያገገሙ፤ የ40 ሰዎች ህይወት አልፏል፤ 2 ሰዎች ወደ ሀገራቸው ጃፓን መመለሳቸው ይታወሳል።

#FBC

የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.