Fana: At a Speed of Life!

አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ በጉራጌ ዞን በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ቦታ ተረከበ

አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 11 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ አስተዳደር በሆቴል ኢንቨስትመንት ለመሰማራት 5 ሺህ 352 ካሬ ሜትር ቦታ መረከቡ ተገለፀ፡፡

በዞኑ በኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚደረግም ተገልጿል።

የከተማው ከንቲባ አቶ እንዳለ ገብረመስቀል በቦታው ርክክብ ወቅት ÷ የከተማ አስተዳደሩ በአትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ በወልቂጤ ከተማ በሆቴል ኢንቨስትመንት ለመሰማራት ያቀረበውን ጥያቄ በደስታ ተቀብሎታል ብለዋል።

አትሌት ሃይሌ የሆቴል ግንባታ እንዲያካሂድ 5 ሺህ 352 ካሬ ሜትር ቦታ እንደተሰጠው ገልጸው÷ ከተማ አስተዳደሩ በቀጣይ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።

የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የፋይናንስ ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አበበ አመርጋ በበኩላቸው÷ የአትሌት ሻለቃ ሃይሌ በኢንቨስትመንት ዘርፍ ለመሰማራት ወደ ወልቂጤ ከተማ መምጣት ሌሎች ባለሃብቶችን ለመሳብ ዕድል የሚፈጥር ነው ብለዋል።

አቶ አበበ  አያይዘውም የወልቂጤ ከተማ ከተቆረቆረች ረዥም ዓመታትን ያስቆጠረች እንደመሆኗ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች ቁጥር ውስን መሆናቸውን ተናግረው÷ የሚገነባው ሆቴልም ይህንን ችግር የሚቀርፍ እንደሚሆን እምነት እንዳላቸውም ጠቁመዋል።

በተጨማሪም ዞኑ ለኢንቨስትመንት ምቹ መሆኑንና በየትኛውም የኢንቨስትመንት አማራጮች ለሚሰማሩ ባለሃብቶች ተገቢውን ድጋፍ ለማድረግ ዞኑ ዝግጁ መሆኑንም አስረድተዋል።

አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ በበኩሉ÷ ለተደረገለት ትብብር አመስግኖ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል በመገንባት ለበርካታ ዜጎች ጊዜያዊና ቋሚ የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጿል።

በዞኑ የተለያዩ አካባቢዎች በሌሎች የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ እንደሚሰማራም አመልክቷል።

የኢፌዴሪ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋም÷  አትሌቱ ከሩጫውም ባለፈ በልማቱ እያደረገ ያለው አስተዋጽኦ በአገራችን ለሚገኙ ለሌሎች ባለሃብቶችም አርአያና ግንባር ቀደም በመሆኑ ሌሎቹም የእሱን ፈለግ መከተል አለባቸው ሲሉ  ገልጸዋል።

አንዳንድ በዕለቱ የተገኙ የወልቂጤ ከተማ ባለሃብቶችና ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት ታዋቂው የሃገራችን አትሌት ወደ ወልቂጤ ለማልማት መምጣቱን እጅግ እንዳስደሰታቸው ገልፀው ስራው በታቀደለት መሰረት እንዲያልቅ የከተማ አስተዳደሩ ተገቢውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባም መግለጻቸውን ከጉራጌ ዞን መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.