Fana: At a Speed of Life!

አንድ ወደፊት ስንሄድ ሁለት ወደኋላ የሚመልሱንን ሀይሎች ማስቆም አለብን-ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 23፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) አንድ ወደፊት ስንሄድ ሁለት ወደኋላ የሚመልሱንን ሀይሎች ማስቆም እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ አሳሰቡ።

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በዛሬው እለት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጥተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በመግለጫቸውም ከሰሞኑ በተከሰተው ግጭት የ86 ሰዎች ህይወት አልፏል ያሉ ሲሆን፥ ከሟቾች መካከል 82 ወንድ፣ 4 ሴቶች መሆናቸውምን አስታውቅዋል።

በብሄር ደግሞ 50 ኦሮሞ፣ 20 አማራ፣ 8 ጋሞ፣ 2 ስልጤ፣ 1 ጉራጌ፣ 2 ሀዲያ እና አንድ አርጎባ ሲሆኑ፥ የአንዱ ሟች ብሄር እንዳልታወቀም አስታውቀዋል።

በሀይማኖት ደግሞ ከሟቾቹ መካከልም 40 ክርስቲያን ሲሆኑ፥ 34 ሙስሊም እና 12 የሌላ እምነት ተከታዮች መሆናቸውንም ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ በመግለጫቸው ያስታወቁት።

ከሟቾቹ መካከል 76 ሰዎች በእርስ በእርስ ግጭት፤ 10 ሰዎች ደግሞ በፀጥታ ሀይሎች ህይወታቸው ማለፉንም ገልፀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ በመግለጫው፥ ይህ ክፉ ክስተት በኢትዮጵያ የግጭት እሳት ሲነሳ አንዱን ክፍል አቃጥሎ ሌላውን አሙቆ የሚያልፍ እንዳልሆነ ያሳየ ነው ብለዋል።

መንግስት የፖለቲካ እና የዴሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት በማሰብ ሆደ ሰፊነቱን አብዝቶ ሲያስታምም ከርሟል ብለዋል።

ከሀይልና ጉልበት ይልቅም፤ ትምህርት እና ምክክር ይሻላል ብሎ መታገሱን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ፥ ትእግሰቱ ፍርሃት፤ ማስታመሙ ድካም፣ የመሰላቸው ካሉ ግን ተሳስተዋል ብለዋል።

አንዳንዶች እንዲማሩ ተብሎ ሰፊ ልብ እና ትክሻ ሲሰጣቸው አጋጣሚውን ሳይጠቀሙበት ቀርተው የዜጎች ህይወት ለአደጋ የሚጋለጥበት ምክንያት መፈጠሩንም አንስተዋል።

መንግስት የዜጎችን እና የተቋማትን ደህንነት ለመጠበቅ የሀገሪቱ ህግ ባስቀመጠው መሰረት እንደሚሰራም አስታውቀዋል።

በአንድ በኩል የፖለቲካውን እና የዴሞክራሲውን ምህዳር ለማስፋት፤ በሌላ በኩል ደግሞ ፍትህንና የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ እንደሚሰራም አስታውቅዋል።

“ያለፉትን ስህተቶች ለማረም እየሰራን በሌላ በኩል ደግሞ ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ ህጋዊና ተመጣጣኝ እርምጃ እንወስዳለን” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ፥ በዚህ አግባብም አልሚ ሁሉ ስራውን፤ አጥፊ ሁሉ ደግሞ በጥፋቱ ልክ ተጠያቂ እየሆነ እንደሚሄድም አስታውቅዋል።

የሀይማኖት አባቶች፣ የጎሳ መሪዎች፣ የፖለቲካ ልሂቃን፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ እናቶች፣ ወጣቶች እና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች መንግስት የሀገሪቱን ሰላም፣ ደህንነት እና አንድነት ለማስጠበቅ ሲል ህግና ስርዓትን እንዲያስከብር ደጋግመው መጠየቃቸውን በማንሳት፥ ጥያቄያቸው ተገቢ መሆኑን እና መንግስትም ህግ የሚፈቅድለትን ሁሉ ለማድረግ አቅምም፣ ዝግጁነትም፣ ብቃትም እንዳለው አስታውቅዋል።

የፀጥታ አካላትም የሀገርን ሰላም፣ ደህንነት፣ የህዝቦችን አብሮ መኖርና አንድነት፣ የተቋማትንና የኢንዱስትሪዎችን ደህንነት በህግ አግባብ የመጠበቅ ግዴታቸውን እንዲወጡም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አሳስበዋል።

የፍትህ አካላትም ለአጥፊዎች ትምህርት፤ ለተጎጂዎች ካሳ የሚሆን የተፋጠነ ፍትህ በማስፈን ፍትህን እንዲያረጋግጡ ጥሪ አቅርበዋል።

ዋልታ ረገጥ የብሄር እና የእምነት ጫፍ ላይ ቆመው ችግሮችን የሚያባብሱ ወገኖችም አስተያየቶቻቸው እና መልእክቶቻቸው ተጨማሪ እልቂትና ጥፋት ከሚያመጣ ማናቸውም ተግባር እንዲቆጠቡም አሳስበዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ፥ “ነገሩን ሁሉ በስሜትና በወገንተኝነት መለኪያ ብቻ ሳንመለከት፤ ከስሜት በላይ ሆነን የተጋረጠብንን አደጋ በብልሃት መቀልበስ እንድንችል የዘወትር ትብብራችሁ እልዳይለየን እጠይቃለሁ” ብለዋል።

በአላዛር ታደለ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.