Fana: At a Speed of Life!

አፍሪካ የኮሮና ቫይረስ ክትባት ፈዋሽነቱ ሲረጋገጥ 220 ሚሊየን ክትባት ታገኛለች – የዓለም ጤና ድርጅት

አዲስ አበባ፣ ነሃሴ 29፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የዓለም ጤና ድርጅት የኮሮና ቫይረስ ክትባት ፈዋሽነቱ ሲረጋገጥ አፍሪካ 220 ሚሊየን መጠን ክትባት እንደምታገኝ አስታወቀ።

የድርጅቱ የአፍሪካ ፕሮግራም አካባቢያዊ ኋላፊ ሪቻርድ ሚሂይጎ እንደገለጹት፥ በቅድሚያ የህክምና ባለሙያዎችና ተጋላጭነት ያላቸው አካላት ይከተባሉ ብለዋል።

ኋላፊው የክትባቱ ፈዋሽነት እንደተረጋገጠ አገራት ባላቸው ህዝብ ቁጥር መሰረት ይሰራጫል ብለዋል።

በአህጉሪቷ ያሉ 54ቱ አገራትም ክትባቱን ለማግኘት እየተጠባበቁ መሆናቸውንም አንስተዋል።

ኮቫክስ የተሰኘ የኮሮና ቫይረስ ክትባት ለማግኘት ዓለም አቀፍ ጥረት መኖሩ የሚታወስ ሲሆን፥ አህጉሪቷም ከዚህ ጥምረት ነው የምታገኘው ተብሏል።

ጥምረቱ እስከ 2021 መጨረሻ ድረስ በዓለም ዙሪያ 2 ቢሊየን መጠን የኮሮና ቫይረስ መከላከያ ክትባት እንደሚያሰራጭ ተነግሯል።

ጥምረቱ እስከ አሁን 9 የተለያዩ የኮሮና ቫይረስ ክትባት ሙከራዎችን እያካሄደ ሲሆን፥ ከዘጠኙ ሁለቱ በአፍሪካ በሙከራ ላይ እንደሚገኙ ተገልጻል።

ምንጭ:-ቢቢሲ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.