Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ ሃብቷን የማልማት ሙሉ መብት  አላት – የደቡብ ሱዳን የውሃ ሃብትና መስኖ ሚኒስትር

አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 24 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በደቡብ ሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ነቢል ማህዲ ከደቡብ ሱዳን የውሃ ሃብትና መስኖ ሚንስትር ከማናዋ ፒተር ጋትኩት ጋር ውይይት አድርገዋል።

አምባሳደር ነቢል በውይይቱ ወቅት ደቡብ ሱዳንና ኢትዮጵያ ጠንካራ ወዳጅነት ያላቸው መሆኑን በማስታወስ በቀጣይ በኢኮኖሚና በልማት መስኮች የበለጠ ማስተሳሰር ተገቢ መሆኑን ለሚኒስትሩ ገልጸውላቸዋል።

በተጨማሪም የሕዳሴ ግድብ ያለበትን ሁኔታ ገለጻ በማድረግ ፤ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ ከኢትዮጵያ አልፎ ለጎረቤት ሃገራት በጎ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል።

ከግድቡ ጋር ተያይዞ ከታችኞቹ ተፋሰስ ሃገራት ጋር ያለው ልዩነት በአፍሪካ ኀብረት ማዕቀፍ በሦስትዮሽ ድርድር እንዲፈታ ኢትዮጵያ ያላትን አቋምም አስረድተዋል።

በተያያዘም የናይል ተፋሰስ ሃገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ ለተፋሰሱ ሃገራት ጠቃሚ መሆኑን ገልጸዋል።

ሚኒስትሩ ማናዋ ፒተር በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳን ያበረከተችው አስተዋጽኦ ታላቅ መሆኑንና እስካሁንም በተለያዩ መስኮች ጠንካራ ድጋፍ እያደረገች መሆኑን በማውሳት አመስግነዋል።

የሕዳሴ ግድብን በተመለከተ መንግሥታቸው ኢትዮጵያ ሃብቷን የማልማት ሙሉ መብት እንዳላት እንደሚያምን እንዲሁም ከታቸኛው ተፋሰስ ሃገራት ጋር ያለው ልዩነት በድርድር መፍታት እንደሚገባ ገልጸዋል።

የናይል ተፋሰስ ሃገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት በተመለከተ የሃገሪቱ ፓርላማ በቅርቡ ሲከፈት እንደሚጸድቅ ሚኒስትሩ ማረጋገጣቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.