Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ ነባሮቹን የ10፣ የ50 እና የ100 የብር ኖቶች የሚተኩ አዲስ የገንዘብ ዓይነቶችና አዲሱን የ200 ብር ኖት ይፋ አደረገች

አዲስ አበባ፣ መስከረም 4፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ ነባሮቹን የ10፣ የ50 እና የ100 ብር ኖቶች ዓይነቶችን ሙሉ ለሙሉ በመተካት ለግብይት የሚሆን አዲስ የብር ኖት መጠቀም እንደምትጀምር ይፋ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ አስታወቁ።

ነባሮቹን የብር ኖቶች ከሚተኩት በተጨማሪ በዛሬው ዕለት የ200 ብር ኖት ይፋ እንደሆነ ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ በፌስቡክ ገፃቸው ባወጡት መረጃ የገለፁት።

የ5 ብር ኖት ባለበት ቀጥሎ፤ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ወደ ሣንቲም የሚለወጥ ይሆናል ተብሏል።

እነዚህ አዲስ የገንዘብ ዓይነቶች ለሕገ ወጥ እንቅስቃሴዎች የሚደረግን ድጋፍ፣ ሙስናን እና የኮንትሮባንድ ሥራዎችን ለመቀልበስ እንደሚረዱ ተጠቁሟል።

እንዲሁም የፋይናንስ ተቋማት የገንዘብ እጥረትን ለመቋቋም እንዲችሉም ያግዛል ነው የተባለው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲሶቹ የገንዘብ ዓይነቶች ላይ የተካተቱ መለያዎች አመሳስሎ ገንዘብ ለማተም የሚደረጉ ሕገ ወጥ ጥረቶችንም ለማስቀረት እንደሚያግዙ ገልፀዋል።

አዲስ የታተሙት የብር ኖቶቹ በአካላቸው ላይ የሚገኙ የደህንነት መጠበቂያ ምልክቶች ያሉባቸው ናቸው።

እነዚህን ያላሟሉ ወይም ተመሳስለው የተዘጋጁ ገንዘቦች የያዙ ወይም የሚጠቀሙ ግለሰቦች ካጋጠሙ ለፀጥታ አካላት መጠቆም እንደሚገባ ተነግሯል።

በአሁኑ ወቅት የአዲሶቹ የብር ኖቶች አብዛኛው የህትመት ሥራ ተገባዶ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ግምጃ ቤት እንደሚገኝ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

የስርጭት ስርዓት እና ዕቅድ የተዘጋጀ ሲሆን፣ በሚመለከታቸው አካላት አማካኝነት እንደሚተገበር ተጠቁሟል።

በገንዘብ ቅያሬው ሂደት የጸጥታ ማስከበር አካላት ከፍተኛ ሚና እንደሚኖራቸው የተገለፀ ሲሆን፥ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ከማህበረሰቡ ጋር በመተባበር ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ እንደሚያስፈፅሙ ተነግሯል።

ለዚህም ከብሔራዊ መከላከያ ሠራዊት፣ ከብሔራዊ የመረጃ እና ደህንነት አገልግሎት እና ከፌደራል ፖሊስ የተውጣጣ ኮማንድ ፖስት ተቋቁሞ፤ ሂደቱን በበላይነት ያስተባብራል።

እንዲሁም የክልል መንግሥታት ተመሳሳይ ኮማንድ ፖስት አቋቁመው ሥራውን እንዲያከናውኑ ይጠበቃል።

የገንዘብ ቁጥሮቹ በሚያጎላ መሳሪያ ሲታዩ ከጥቁር ወደ አረንጓዴ ፍሎረሰንት ቀለም እንደሚለወጡ ብሄራዊ ባንክ አስታውቋል።

ለአይነ ስውራንም የእውቅና ምልክት ያለው ሲሆን የብሩን ዋጋ በእጅ ዳሰሳ ማወቅ የሚችሉበት የደህንነት መጠበቂያ ያለው ነው።

በተመሳሳይ ገንዘቡ ወደ ላይ ወይንም ወደታች ሲዞር የሚንቀሳቀስ ደማቅ የቀለም ፍንጣቂ የደህንነት መጠበቂያ ምልክት እንዳለውም ነው ተነግሯል።

የብር ኖቱ ሲዳሰስ የመጎርበጥ ስሜት እንዲሁም የኖቱ ዋጋ ይታያል።

የሚሽከረከር ደማቅ ቀለም ኮኮብ አዲስ የደህንነት መጠበቂያ ክር፤ በክሩ ውስጥም NBET፣ ኢብባ እና ገንዘቡ አይኖቶች ተፅፈው ይገኙበታል ነው የተባለው።

ገንዘቡ ወደ ብርሃን አቅጣጫ ተደርጎ ሲታይ በላይ ላይ ከሚገኘው ምስል ፊት ለፊት ተመሳሳይ ደብዛዛ ውሃ መልክ ያለው ምልክት እንደሚታይ ተጠቁሟል።

የብር ኖቶቹ በብርሃን አቅጣጫ ሲታዮ ኳስ መሳይ ምልክት ከኖቶቹ በስተኋላ ካለው ተመሳሳይ ምልክት ጋር በፍፁም ትይዩ ሆነው በአንድ ቦታ ላይ ያርፋሉ።

እንዲሁም አንበሳው ምስል ራስ ላይ አልትራቯዮሌት ጨረር ሲበራበት ወደ ቢጫነት የሚለወጥ ፍሎረሰንት ምልክት አለው ተብሏል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.