Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ድርድር ከመጭው ክረምት በፊት ይጠናቀቃል የሚል እምነት እንዳላት አቶ ደመቀ መኮንን ገለጹ

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 19 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ድርድር ከመጭው ክረምት በፊት ይጠናቀቃል የሚል እምነት እንዳላት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገለጹ፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከኖርዌይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢኔ ኤሪክሰን ሶሬይድ ጋርተወያይተዋል፡፡

በዚህ ወቅትም በትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ እና የታላቁ የህዳሴ ግድብ ድርድርን በተመለከተ ለሚኒስትሯ ገለጻ አድርገውላቸዋል፡፡

ከግድቡ ጋር በተያያዘ ያለውን ድርድርም ኢትዮጵያ ድርድሩን በቅንነት እያደረገች መሆኗን አስረድተዋል፡፡

አቶ ደመቀ በማብራሪያቸው በኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብጽ እየተካሄደ ያለው የሶስትዮሽ ድርድር ግድቡን ለመሙላት ከታሰበበት መጭው ክረምት በፊት ይጠናቀቃል የሚል እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡

በትግራይ ክልል ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ በሰጡት ማብራሪያም፥ ማንኛውን የረድኤት ድርጅት በክልሉ መንቀሳቀስና ሰብአዊ ድጋፍ ማድረስ እንደሚችል አስረድተዋል፡፡

አሁን ላይ በክልሉ የሰብአዊ አቅርቦቱ መሻሻሉን ያነሱት ሚኒስትሩ፥ በክልሉ መሰረታዊ አገልግሎቶች በመደበኛነት መጀመራቸውንና የመንግስት ሰራተኞች ደመወዝም እየቀረበ መሆኑን አውስተዋል፡፡

በክልሉ እስካሁን 3 ነጥብ 1 ሚሊየን የሚሆኑ ዜጎች ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁሶች ድጋፍ ማግኘታቸውንና ከዚህ ውስጥ መንግስት 70 በመቶውን እንደሸፈነም ጠቅሰዋል፡፡

በአካባቢው አለ ከተባለው የሰብአዊ መብት ጥሰት ጋር በተያያዘም መንግስት ከፌደራል ፖሊስ እና ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ባለሙያዎችን በስፍራው በማሰማራት ጉዳዩን እያጣራ ነው ብለዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞም መንግስት ተሳትፎ አላቸው የተባሉ አካላትን ለህግ ለማቅረብ ቁርጠኛ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.