Fana: At a Speed of Life!

ከመንግስት የፀጥታ አካላት ውጪ ማንኛውም አካል የጦር መሳሪያ ታጥቆ መንቀሳቀስ የለበትም – አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ

የአዲስ አበባ፣ ህዳር 19፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በመንግስት እውቅና ካላቸው የፀጥታ አካል ውጪ ማንኛውም አካል የጦር መሳሪያ ታጥቆ ህብረተሰቡ ውስጥ መንቀሳቀስ እንደሌለበት የኦሮሞ አባ ደጋዎች ህብረት ሰብሳቢ እና የጉጂ አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ ውሳኔ አሳለፉ።

የኦሮሞ አባ ደጋዎች ህብረት ሰብሳቢ እና የጉጂ አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ፥ በደቡብ ኦሮሚያ አካባቢ መሳሪያ ታጥቆ ህዝብን እያሰቃየ ያለውን ቡድን አስመልክቶ ውሳኔ አሳልፈዋል።

የኦሮሞ አባ ደጋዎች ህብረት ሰብሳቢ እና የጉጂ አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ በአካባቢው በሚስተዋለው የፀጥታ ችግር ዙሪያ በዛሬው እለት በተካሄደ የውይይት መድረክ ላይ ነው ውሳኔውን ያሳለፉት።

በውሳኔያቸውም በመንግስት እውቅና ካላቸው የፀጥታ አካል ውጪ ማንኛውም አካል የጦር መሳሪያ ታጥቆ ህብረተሰቡ ውስጥ መንቀሳቀስ እንደሌለበት አሳውቀዋል።

የኦነግ ሸኔ ታጣቂ ኃይል በተለይ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የሚያደርሰውን እንግልት ከግንዛቤ በማስገባት ኦሮሞ የሆነ ሰው ሁሉ ከዚህ ታጣቂ ኃይል ጋር ያለውን ግንኙነት በአስቸኳይ እንዲያቋርጥ አባ ገዳው ውሳኔ አስተላልፈዋል።

በኦሮሞ ላይ አፈ-ሙዝ አዙሮ የሚወጋ የትኛውም ወገን ኦሮሞነቱ መሰረዝ እንዳለበትም አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ አስታውቀዋል።

የኦነግ ሸኔ ታጣቂ ኃይል የኦሮሞን ባህል እና ወግ በመተላለፍ ከሁለት ዓመታት በፊት በገዳ የተላለፈውን አዋጅ በመጣስ የኦሮሞ ሕዝብ ለባህሉ ያለውን ክብር ያዋረደ በመሆኑ ሕዝቡ ከአሁን ወዲህ ሊነቃ ይገባል ማለታቸውን ኦቢኤን ዘግቧል።

ይህ ታጣቂ ኃይል በታላቁ የኦሮሞ ሕዝብ ባህል መሠረት ተመክሮ ከጥፋቱ ሊመለስ ባለመቻሉ “ጠላት” የሚል ስያሜ ሊሰጠው እንደሚገባም ነው አባ ገዳ ጂሎ ማንዶ የገለጹት።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.