Fana: At a Speed of Life!

ከወንበዴው ህወሓት የጥፋት ተልዕኮ ተቀብለው በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በህዝብ እልቂት በማድረስ አገርን ለማፍረስ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የጥፋት ቡድኖች በቁጥጥር ሥር ዋሉ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 27፣ 2013 (ኤፍ.ቢሲ) ከወንበዴው ህዋሃት የጥፋት ተልዕኮ ተቀብለው በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በህዝብ እልቂት በማድረስ አገርን ለማፍረስ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የጥፋት ቡድኖች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት አስታወቀ፡፡
የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ጉዳዩን አስመልክቶ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው ከወንበዴው ህዋሃት የጥፋት ተልዕኮ ተቀብለው በጋምቤላ ክልል በብሔር ብሄረሰቦች መካከል ግጭት በመፍጠር አካበቢውን የትርምስ ቀጠና ለማድረግ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሀይሎች በተደረገባቻው ጥብቅ ክትትል በቁጥጥር ስር መዋላቸውን አስታውሷል፡፡
የዚህ የጥፋት ቡድን አካል የነበሩ ነገር ግን ወደ አዲስ አበባ በመምጣት ተልዕኮቸውን በድብቅ ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ የነበሩ አለም ደስታ ሃየሎምና ጋትክቦም የተባሉ የጥፋት ቡድኑ ተጠርጣሪዎች ባሉበት ታድነው በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል፡፡
ቀደም ሲል ይፋ በተደረገው መረጃ ላይ እንደተመለከተው፤ በህዝብ ላይ እልቂት በመፈጸም ክልሉን የትርምስ ቀጠና ለማድረግ ሲንቀሳቀሱ ከነበሩት ተጠርጣሪዎች መካከል ጸጋዬ መብርሃቱ (ካህሳይ)፣ ገብረማሪያም አናንያ፣ ዋስትና ተሾመ (ጃል ሴና)፣ አብርሃም መሃሪ፣ ኮሎኔል ተስፋዬ (ባሌስትራ) እና በድምሩ 19 የወንበዴው የህዋሃትና የኦነግ ሸኔ የጥፋት ኃይሎች በቁጥጥር እንደዋሉ መግለጫው አስታውሷል።
በተመሳሳይ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን ተፈጽሞ የነበረውን ተመሳሳይ ጥፋት በአሶሳና ካማሼ ዞኖች ብሔር ብሄረሰቦችን በማጋጨት አካበቢውን የትርምስ ቀጠና በማድረግ በህዝብ ላይ እልቂት ለመፈጸም ከወንበዴው ህዋሃት የጥፋት ቡድን አባል ከሆነው አባይ ፀሃዬ ተልዕኮ ወስደው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ተጥራጥሪዎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ መገለፁ ይታወቃል፡፡
የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መግለጫ እንዳመለከተው፤ በተጨማሪም አራት የወንበዴው የህዋሃት የጥፋት ቡድን አባላት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ተደርጓል።
የተያዙት አራት የዚህ የጥፋት ቡድን አባላት ተጠርጣሪዎችም ተክላይ ገብረ መድህን ፣ ፍሰሃ ወልደ እግዚአብሄር ፣ አብርሃ ገብረ ሚካኤል እና ተስፋ ገብረ ሚካኤል የተባሉ መሆናቸውን አገልግሎቱ በላከው መግለጫ አስታውቋል።
ከወንበዴው ህዋሃት የጥፋት ቡድን ተልዕኮ በመቀበል በህዝብ ላይ ጭፍጨፋ እንዲፈጸም ስምሪት የተሰጣቸው አራት ከላይ የተገለፁት የጥፋት ሃይሎች በእጃቸው 59 የሚሆኑ የባንክ ደብተሮችን የያዙ ሲሆን፤ ተክላይ ገብረ መድህን የተባለው ተጠርጣሪ በአገር ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ ባንኮች 19 የሂሳብ ደብተሮችን ከፍቶ ሲያንቀሳቅስ ከመቆየቱም በላይ በአንዱ የሂሳብ ደብተር ውስጥ ብቻ ከ12 ሚሊዮን ብር በላይ መገኘቱን መግለጫው ጠቁሟል ።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የማነ ግርማይና ዮሃንስ ግርማይ የተባሉ የህዋሃት የጥፋት ቡድን ተላላኪዎችን ጨምሮ በድምሩ 23 ተጠርጥሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት አስተውቋል፡፡
ከወንበዴው ህዋሃት የጥፋት ቡድን ተመሳሳይ ተልዕኮ ተቀብለው በአዲስ አበባ ከተማና በዙሪያው በከፍተኛ ባለስልጣናትና በንፁሃን ዜጎች ላይ እንዲሁም በትላልቅ መሰረተ ልማቶች ላይ ለአብነትም ለገዳዲና ገፈርሳ የሚገኙ የውሃ ግድቦች እንዲሁም በለገጣፎ የሚያልፍ ከፍተኛ የውሃ ማስተላለፊያ መስመር ላይ የፈንጂ ጥቃት ለመፈጸም ዝግጅት ሲያደርጉ የቆዩ የኦነግ ሸኔ አባላት ለጥፋት ተልዕኳቸው ካዘጋጇቸው ተቀጣጣይ ፈንጂዎችና ሌሎች ቁሶች ጋር በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ብሄራዊ መረጀና ደህንነት አገልግሎት በላከው መግለጫ ገልፆል፡፡
የጥፋት ተልዕኮቸው ባይከሽፍ ኖሮ፤ በህዝቡ ላይ ከፍተኛ ማህበራዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ሰብኣዊ ቀውስ ያስከትል እንደነበር መግላጫው አስታውሷል፡፡
የዚሁ ጥፋት አካል የነበሩትና የጥፋት ቡድኑ ያሰማራቸው ቶሎሳ አብዲሳ፣ ደጀኔ ፍቃዱ፣ ሀብታሙ ተስፋየ መርጋ፤ ንጉሴ አሰፋና ፈልማት ታከለ የተባሉ ተጠርጣሪዎች መሆናቸውን መግላጫው አመልክቷል፡፡
በሌላም በኩል ጋዲሳ ሞሲሳ ባይሳ የተባለው የጥፋት ቡድኑ አካልና ግብርአበሮቹ በአዲስ አበባ በንጹሃን ዜጎች ላይ የቦንብ ጥቃት ለመፈጸም ካዘጋጇቸው ቦንቦች ጋር በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት አስተውቋል፡፡
በተለይ የወንበዴው የህዋሃት ቡድን ለጥፋት ተልዕኮው ሽፋን ንስር ጥበቃ ድርጅትን በመጠቀም በስራቸው ከወንበዴው ስልጠና የወስዱ ሃይሎችን በስሩ በማደራጀት በንፁሃን ዜጎች ላይ ጥቃት ለመፋፀምና ጥፋት ለማድረስ በዝግጅት ላይ እያሉ በቁጥጥር ስር እንዲውሉም ተደርጓል፡፡
የህዋሃት የጥፋት ቡድን በትግራይ ክልል ሃግቦ በተባለ አካባቢ ወታዳራዊ ስልጠና በመስጠት የገዳይ እስኮድ ቡድን ባለቤትነቱ ሀይሉ በርሄ በቅፅል ስሙ ሀይሉ ሳንቲም ተብሎ በሚጠራው የወንበዴው የጥፋት ቡድን አስተባባሪ ስም በተቋቋመው ንስር የግል ጥበቃ ኤጀንሲ ሽፋን ካስገባ በኃላ ነበር ጥቃት ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ ብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ከፌደራል ፖሊስና ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጋር በቅንጅት ባደረጉት ጥብቅ ክትትል የቡዱኑ አባላትን በቁጥጥር ስር ማዋል የተቻለው፡፡
በተመሳሳይ አዲስ አበባ ሆኖ ለወንበዴው ለህዋሃት የጥፋት ቡድን የተለያዩ መረጃዎችን እያሰባሰበ ሲልክ የነበረና ከኦሮሚያ ወጣቶችን እየመለመለ ለስልጠና ወደ ትግራይ በመላክና የተለያዩ የአመፅ ተልዕኮዎችን ከጥፋት ቡድኑ በመቀበል ኦሮሚያ ክልል ለሚገኙ የኦነግ ሸኔ የጥፋት ቡድኖች ሲያስተላልፍ የነበረው ቶማስ ገብረማሪያም የተባለው ተጠርጣሪም በቁጥጥር ስር እንዲውል ተደርጓል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የጥፋት ቡድኑ በኦሮሚያ ክልል በአዳማ፤በሲዳማ ክልል ሃዋሳ፤በደቡብ ክልል ደግሞ በወላይታ፤ ጋሞጎፋ፤ሃድያ፤ስልጤና ጌዲዮ ዞኖች እንዲሁም በሱማሌ ክልል ጅጅጋና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ተመሳሳይ ትርምስና እልቂት በተላላኪዎች ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ በድምሩ 21 ተጠርጣሪዎች በተለያዩ የጡር መሳሪዎችና መሰል ቁሳቁሶች ጋር በቁጥጥር ስር እንዲውሉ መደረጉን አግልግሎት መስሪያ ቤቱ አስታውቋል፡፡
በመጨረሻም ለዚህ ኦፕሬሽን ስኬት የአገራችን ህዝቦች ተሳትፎ የማይተካ ሚና ያለው ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ ብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት፤ የአገር መከላከያ ሰራዊት፤የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፤የክልል ፖሊስ ኮሚሽኖችና ሌሎች የጸጥታ አካላት በቅንጅት ይሄ ዉጤት እንዲመጣ ግዴታቸውን ተወተዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.