Fana: At a Speed of Life!

ወርቃማ ድል የተጎናጸፍነው ትልቁን ስዕል ማየት የሚችሉ ፣ ችግሮቻቸውን የመፍታት ልምድ ያላቸው እናትና አባቶች ስላሉን ነው – ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 23፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ)”በስልጡን ምክክር አዲስ ተስፋ ምዕራፍ “በሚል መሪ ሀሳብ ለሶስት ተከታታይ ቀናት  ሲካሄድ የነበረውን የምክክር መድረክ የማጠቃለያ ፕሮግራም በወዳጅነት አደባባይ  ተካሂዷል።

በዚህ መርሃ ግብር ላይ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴን ጨምሮ ፣የክልል ርእሳነ መስተዳድራን፣ ሚኒስትሮች ፣ ከፍተኛ መንግስት የስራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የውጭ አገራት ተወካዮችም   ተገኝተዋል።

በመድረኩም ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ባደረጉት ንግግር እኛ ኢትዮጵያውያን ከ125 ዓመታት በፊት በአባቶችና እናቶች በፅናት ተሳስረን እስከ ዛሬ ሳንፈታ ቆይተናል ብለዋል፡፡

ይህንን ወርቃማ ድል የተጎናጸፍነው ትልቁን ስዕል ለማየት የሚችሉ ፣ በዋርካ ስር ቁጭ ብለው ችግሮቻቸውን የመፍታት ልምድ ያላቸው እናትና አባቶች ስላሉን ነው ሲሉ ገልጸዋል።

እስከዛሬ የገጠሙንን ሁሉ ያለፍናቸው እንደ አንድ ልብ መክረን ነውና ምክክር ባህላችን ብቻ ሳይሆን ስሪታችንም ጭምር   በመሆኑ ነው  ብለዋል።

የአባቶቻችን ድል  ከአድዋ ድል 40 ዓመት በኋላ የመጣብን ፈተና እና እሱን ተከትሎ የገጠመን ድርቅና ረሀብ፣ የተፈጥሮም ሆነ የሰው ሠራሽ ፈተና መቋቀም አስችሎናልም ነው ያሉት ።

ላለፉት 6 ወራትም ሆነ በእነዚህ ሦስት ቀናት በመደማመጥ፣ በመመካከር እና በመረዳዳት በተደረገው ምክክር የአድዋ መንፈስ አሁንም አብሮን እንዳለ በርግጥም ታይቷል  ሲሉ ገልጸዋል።

አያይዘውም ተሰባስበን ስንመክር ለሌላውም መትረፍ እንችላለን  ሲሉ  ገልጸዋል

የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪሃት ካሚል በበኩላቸው ÷የአድዋ ድል ኢትዮጵያ ለዓለም ፍትሕ ፈላጊ ሕዝቦች ካበረከተቻቸው ስጦታዎች አንዱና ዋነኛው ነው ብለዋል።

ብሔራዊ መግባባት መፍጠር ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ሥራው ትልቅ ትርጉም አለውም ነው ያሉት ።

በአድዋ ድል ሕብረ ብሔራዊነት ችግር እንዳልሆነ በተጨባጭ የታየበት መሆኑን አስታውሰው ÷ ዝቅ ብለን ኢትዮጵያን ወደላይ ከፍ ማድረግ የሚጠይቀን ወቅት ላይ ነው የምንገኘው ሲሉ ገልጸዋል።

ዜጎች በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ከቻሉ የአገር ግንባታ ሥራው ደረጃ በደረጃ የሚከወን መሆኑን አመልክተዋል።

የምክክር መድረኩ  ከየካቲት 20 እስከ 22 ቀን 2013 ዓ.ም ለሶስት ተከታታይ ቀናት የተካሄደ ሲሆን÷ የምክክር መድረክ አስመልክቶም  የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪሃት ካሚል ዛሬ መግለጫ መስጠታቸው ይታወሳል ።

በዚህም መግለጫ ከሁሉም የሀገሪቱ  አካባቢዎች ሁሉን የህበረተሰብ ክፍሎች የወከሉ፣ ሁሉንም የፖለቲካ አመለካከቶች የወከሉ ተሳታፊዎች የታዳሙበት  እንደነበር ገልፀዋል።

የሠላም ሚኒስቴር ላለፉት ስድስት ወራት በመላ አገሪቷ የተለያዩ ክፍሎች ከመላ የኅብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ከ20 ሚሊየን በላይ ዜጎች በአገራዊ መግባባት ላይ ብሔራዊ የምክክር መድረኮች አካሂዷል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.