Fana: At a Speed of Life!

የተለያዩ ሀሰተኛ ስሞችንና ሰነዶችን በመጠቀም ሲያጭበረብር የነበረው ግለሰብ በቁጥጥር ስር ዋለ

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 27 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የተለያዩ የስራ ድርሻ፣አድራሻ፣ ስምና ሐሰተኛ ሰነዶችን በመጠቀምና በማጭበርበር ወንጀል የተጠረጠረ ግለሰብ በቁጥጥር ስር መዋሉን የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ግለሰቡ ስንታየሁ ቢርጉ ካየና፣ ስንታየሁ ተመስጌን አበራና ስንታየሁ ደምሴ የተባሉ ስሞችን በመጠቀም የማጭበርበር ተግባር ሲፈፅም መቆየቱን በፋይናንስና ንግድ ነክ ወንጀል ምርመራ ዳይሬክቶሬት የህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ወንጀል ምርመራ ኃላፊ አቶ ሽመልስ ጥበቡ ገልፀዋል፡፡
ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ ይዞ መገኘት፣ማታለልና በባለስልጣን ስም መነገድ ግለሰቡ ከተጠረጠረባቸው ወንጀሎች መካከል ጥቂቶቹ መሆናቸውን አቶ ሽመልስ ተናግረዋል፡፡
በሀሰተኛ መታወቂያው ላይ የፕሮቪዥን ኃላፊ እንደሆነ የሚገልጽ ሰነድ በማዘጋጀት ሲገለገልበት መቆየቱንም ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ የስራ ድርሻው መርማሪ መሆኑን የሚገልጽ ሐሰተኛ መታወቂያ አስወጥቶ ሲገለገል መቆየቱን ፖሊስ ባደረገው ምርመራ እንደደረሰበት ተገልጿል፡፡
በወንጀል ተጠርጣሪ ግለሰቦች ላይ ብርበራ ሲደረግ እንደ ጠቋሚና ተባባሪ ሆኖ በመቅረብ የከፍተኛ መንግስት ባለስልጣናትን ስም እየጠራ ጉቦ የሚጠይቅ መሆኑ መገለፁን ከፌደራል ፖሊስ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
ተክለብርሐን አምባዬ ኮንስትራክሽን ድርጅት በሚያዝያ 19 ቀን 2013 ዓ.ም በመሄድ ድርጅታቹ ሊዘጋ ነው ወይም ሊታገድ ነው ብሎ በማስፈራራት 500 ሺህ ብር ጉቦ መቀበሉንና በህገ-ወጥ መንገድ የተገኘውን ገንዘብም ለማሸሽ ሲል ወደ የባለቤቱ የሂሳብ ደብተር ሲያስተላልፍ እንደነበር ፖሊስ በማስረጃ ማረጋገጥ መቻሉን አቶ ሽመልስ ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ከቴሌ ኮሙዩኒኬሽን የእሱ ባልሆነና ስንታየሁ ደምሴ በሚል ስም የሐሰተኛ መታወቂያ ሲም ካርድ እያወጣ ሲጠቀም መቆየቱን ፖሊስ ባደረገው ምርመራ ያረጋገጠ ሲሆን ግለሰቡ ሲጠቀምባቸው የነበረው መታወቂያዎች ሁሉ ሐሰተኛ መሆናቸውን ፖሊስ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመሆን ባደረገው ምርመራ ማረጋገጡም ተገልጿል፡፡
የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ኢንተለጀንስ በግለሰቡ ላይ ባደረገው ክትትል ግለሰቡን በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በቁጥጥር ስር ያዋለው ሲሆን የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ምርመራ ቢሮም የክስ መዝገቡን ለሚመለከተው አቃቤ ህግ እንደላከ አስታውቋል፡፡
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
.
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.