Fana: At a Speed of Life!

የቻይና ሮኬት ስብርባሪ በኢትዮጵያ ቢወድቅ ምን ዓይነት የጥንቃቄ እርምጃዎች ሊወስዱ ይገባል?

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 30 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ከቁጥጥር ውጪ የሆነው የቻይና ሮኬት አካል ስብርባሪ በኢትዮጵያ ቢወድቅ ምን ዓይነት የጥንቃቄ እርምጃዎች ሊወስዱ ይገባል?።

የቻይናው 5 ቢ ሮኬት ከቁጥጥር ውጪ ሆኖ ወደ መሬት ለመምዘግዘግ ምድርን በመሽከርከር ላይ ይገኛል።

5 ቢ ሮኬት ከቁጥጥር ውጭ ከሆነበት ከሚያዝያ 21 ቀን 2013 ዓ.ም. እንስቶ በከፍተኛ ፍጥነት በመሬት ዙሪያ እየተሸከረከረ እንደሚገኝ  የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስትቲዩቱ አስታውቋል።

ኢንስትቲዩቱ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንዳስታወቀው በመሬት ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅበት ጊዜ 90 ደቂቃ ሲሆን ፍጥነቱም በስዓት 28 ሺህ ኪ.ሜ ይደርሳል ነው ያለው።

እንቅስቃሴው መደበኛ ያልሆነ ሲሆን ከፍታው ከምድር ዝቅ ሲል እስከ 170 ኪ.ሜ. ከፍ ሲል ደግሞ እስከ 370 ኪ.ሜ. ይደርሳል ተብሏል።

በአብዛኛው ከምድር ወገብ ወደ ሰሜን እና ደቡብ 41 ዲግሪ ላትቲዩድ ድረስ እየዋዠቀ መደበኛ የምህዋር መገኛን ሳይጠብቅ ምድርን እየዞረ እንደሚገኝም ነው የተገለፀው።

ሳተላይት ለማምጠቅ ጥቅም ላይ የሚውሉ ሮኬቶችን በሚመለከት የተለመደው አሰራር ተልዕኳቸውን ከጨረሱ በኋላ ከቁጥጥር ሳይወጡ የመሬት ከባቢ አየር ክልልን አልፈው ተገማች በሆነ ስፍራ ወደ ውቅያኖስ ውስጥ እንዲገቡ ወይም ሰው በማይኖርበት ራቅ ያለየመሬት አካል እንዲያርፉ ማድረግ ነው፡፡

ነገር ግን የሎንግ ማርች 5 ቢ ሮኬት ስብርባሪ ከቁጥጥር ውጭ በመሆን ወደ መሬት ለመምዘግዘግ ምድርን በመሽከርከር ላይ ይገኛል።

5ቢ ሮኬት ከቁጥጥር ውጭ ስለሆነበት ምክንያት እስካሁን የተሰጠ የተሟላ ቴክኒካዊ ምክንያት ባይቀርብም ምናልባትም ሮኬቱ ከሚጠበቀው በላይ ከፍታ እንዲወጣ አና ከተለመደው ፍጥነት በላይም እንዲጓዝ በመደረጉ ነው የሚሉ መላ ምቶች እየቀረቡ ነው፡፡

በመሆኑም ሎንግ ማርች ሮኬት ስብርባሪ በኢትዮጵያ ቢወድቅ ምን ዓይነት የጥንቃቄ እርምጃዎች ሊወስዱ ይገባል?

በኢትዮጵያ ላይ ስብርባሪው የማረፍ እድል አለው የለውም የሚለውን እርግጠኛ ሆኖ መናገር የሚቻለው ሮኬቱ መሽከርከሩን አቁሞ ወደ ከባቢ ኣየር መግባት እና ወደ መሬት መምዘግዘግ ከጀመረበት ቅጽበት ኣንስቶ ነው፡፡

ከዚህ ጊዜ እንስቶ ስብርባሪው ወደ መሬት ለመድረስ የሰዓታት ጊዜ ስለሚኖረው ቦታው እንደታወቀ የጥንቃቄ እርምጃዎችን

መውሰድ ይገባል።

ባሉበት አካባቢ ስብርባሪው እንደሚደርስ ከታወቁ በእግርም ሆነ በተሽከርካሪ የሚደረግ እንቅስቃሴን መገደብ፤

ጠንካራ ከለሳ ወይም የላይ ሽፋን ባለው ስፍራ ስር መሆን፣

ድንገት ስራ ላይ ከሆኑ ሔልሜት ማድረግ እና የመሳሰሉትን የጥንቃቄ እርምጃዎች መውስድ ይገባል ሲል ነው ኢንስትቲዩቱ ያስታወቀው ፡፡

በሀይማኖት ኢያሱ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.