Fana: At a Speed of Life!

የአርሲ ዞን እና የአሰላ ከተማ ነዋሪዎች ከ550 በላይ ሰንጋዎችን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ድጋፍ አደረጉ

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 5 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የአርሲ ዞን እና የአሰላ ከተማ ነዋሪዎች ከ550 በላይ ሰንጋዎችን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ድጋፍ አደረጉ።

የህወሓት ጁንታ ቡድን የከፈተውን ጥቃት ለመመከት እና ህግን ለማስከበር የተጀመረውን ዘመቻ እንደሚደግፉም ነዋሪዎቹ አረጋግጠዋል።

የሀገር ደጀንና የኢትዮጵያውያን ሁሉ ለሆነው መከላከያ ሰራዊት የሚያደርጉትን የሞራልና የገንዘብ ድጋፍም እንቀጥላለን ነው ያሉት።

ከዞኑ ሁሉም ወረዳዎችና ከአሰላ ከተማ አስተዳደር ህብረተሰቡ በራሱ ተነሳሽነት ያወጣጣው ድጋፍም ተበርክቷል።

እስካሁን ከ550 በላይ ሰንጋዎች የተሰበሰቡ ሲሆን ሌሎች ወረዳዎችም ተመሳሳይ ድጋፎች ማድረጋቸው ተጠቁሟል።

የአርሲ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ጀማል አልዩ የጥፋት ቡድኑ ተግባር ዜጎችን በአንድ ያቆመ ነው ብለዋል።

በህብረተሰቡ የተፈጠረው ቁጭትም በራሱ ተነሳሽነት ድጋፍ እንዲያደርግ ምክንያት ሆኗል ነው ያሉት።

የአርሲ ዞንና አሰላ ከተማ ነዋሪዎች ዛሬ የህግ ማስከበር ዘመቻውን የሚደግፍ ሰልፍ ያካሂዳሉ።

በአፈወርቅ እያዩ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.