Fana: At a Speed of Life!

የአውሮፓ ህብረት ልዩ መልዕክተኛ ስለ ትግራይ ክልል እውነታ እና ተዓማኒነት የሌለው መግለጫ ሰጥተዋል – አምባሳደር ሂሩት

አዲስ አበባ፣ የካቲት 22፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የአውሮፓ ህብረት ልዩ መልዕክተኛ ፔካ ሃቪስቶ ስለ ትግራይ ክልል መሬት ላይ ባለ ሃቅ ያልተመሰረተ እና ተዓማኒነት የሌለው መግለጫ መስጠታቸውን በቤልጂየም፣ በሉክዘንበርግ እና በአውሮፓ ህብረት ተቋማት የኢትዮጵያ አምባሳደር ዶክተር ሂሩት ዘመነ ገለጹ፡፡

ዶክተር ሂሩት ይህንን ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን መግለጫ መሰረት በማድረግ ዘገባ ለሰራው ለኢዩ ኦብሰርቨር አርታዒ በጻፉት ደብዳቤ ነው፡፡

በደብዳቤያቸውም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ በከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ማብራሪያ እንደተሰጣቸው ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም መንግስት በጉዳዩ ዙሪያ ተጨባጭ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ወደ ትግራይ ክልል እንዲያቀኑ ጉዞ አመቻችቶ እንደነበርም ጠቅሰዋል፡፡

ሆኖም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወደ ክልሉ ለማቅናት ፍላጎት አላሳዩም ነው ያሉት፡፡

ከዚህ ይልቅ ወደ ሱዳን በማቅናት የስደተኞችን ካምፕ መጎብኘታቸውን አስረድተዋል፡፡

በዚያም የኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና ለመፍጠር ያለሙ የተጋነኑ፣ ተጨባጭነት የሌላቸው መሰረተ ቢስ ወሬዎች እንደተናፈሱም አስታውቀዋል፡፡

መንግስት በአሁኑ ወቅት በክልሉ ከሚገኙ 36 ወረዳዎች ውስጥ በ34 ወረዳዎች ከ3 ነጥብ 1 ሚሊየን በላይ ዜጎች ሰብዓዊ እርዳታ ማድረሱን አስታውሰዋል፡፡

ከዚህ በተቃራኒው የሆነው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ መግለጫ በክልሉ ከሚንቀሳቀሱ ዓለም አቀፍ ተቋማት ምልከታ ጋር የሚጻረር ነውም ብለዋል፡፡

ዶክተር ሂሩት በደብዳቤያቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ትክክለኛ መረጃ አለመያዛቸውን ጠቅሰው በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ አፍራሽ ሳይሆን ገንቢ የሆኑ ጉዳዮችን እንደሚያበረታቱ ነው የገለጹት፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.