Fana: At a Speed of Life!

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለጋራ መኖሪያ ቤት ደንበኞቹ የ3 ወራት የብድር መክፈያ እፎይታ ሰጠ

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 8፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ ምክንያት በማድረግ ለጋራ መኖሪያ ቤት ደንበኞቹ የሶሰት ወራት የብድር መክፈያ እፎይታ ጊዜ መስጠቱን አስታወቀ።

በዚህም ባንኩ ከደንበኞቹ መሰብሰብ የሚችለውን ከግማሽ ቢሊየን ብር በላይ ብድር ወደቀጣይ ጊዜ ማስተላለፉን ነው የገለጸው።

የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ ዛሬ በሰጡት መግለጫ ባንኩ መንግስት ነዋሪዎችን የቤት ችግር ለመፍታት ያወጣውን ፖሊሲ መሰረት በማድረግ ላለፉት ዓመታት ከ74 ቢሊየን ብር በላይ በአዲስ አበባ ከተማና በክልል ከተሞች ለፕሮግራም ማስፈጸሚያ ብድር መስጠቱን ገልጸዋል።

በተጫማሪም ነዋሪዎች ከባንኮች ጋር በመቆጠብ የቤት እድለኛ በሚሆኑበት ጊዜ የሚሰጠውን በረጅም ጊዜ የሚከፈል ውል ከ107 ሺህ በላይ ለሆኑ ደንበኞች ከ15 ቢሊየን ብር በላይ ብድር ማቅረቡንም ተናግረዋል።

በአሁኑ ሰዓትም በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ በ40/60፣ በ20/80 እና በ10/90 የመኖሪያ ቤት ልማት መርሐ ግብር ከ31 ቢሊየን ብር በላይ በመቆጠብ የቤት ባለቤት ለመሆን በመጠባበቅ ላይ እንደሆኑ ጠቁመዋል።

በመላው ዓለም የተከሰተው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በጤና፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖ እያሳደረ መሆኑን ገልጸው፤ ደንበኞች በወረርሽኙ ሳቢያ ብድራቸውን በተቀመጠላቸው ጊዜ መክፈል ይቸገራሉ በሚል የብድር መክፈያ ጊዜ እፎይታ ለመስጠት መወሰኑን አብስረዋል።

በዚህም ከሚያዝያ ወር እስከ ሰኔ ወር መጨረሻ መክፈል የሚጠበቅባቸው የሶስት ወራት ክፍያ እንደተራዘመላቸው ይፋ አድርገዋል።

ለዚህም ደንበኞች ባንኩ ቀርበው ምንም አይነት ውል መፈጸም አይጠበቅባቸውም።

ነገር ግን የብድር መክፈያ ጣሪያው እንደማይራዘም ገልጸው፤ ”ክፍያውን መክፈል አቅም ያላቸው ደንበኞች የወርሃዊ ብድር ክፍያቸውን እንዲከፍሉ ይበረታታሉ” ብለዋል።

ባንኩ የብድር መክፈያ ጊዜ እፎይታ በማድረጉ 542 ሚሊየን ብር ገንዘብ መሰብሰብ ይችል እንደነበር ገልጸው፤ ”በወረርሽኙ ምክንያትም ወደቀጣይ ጊዜ አራዝሟል” ነው ያሉት።

ይህ በእንዲህ እንዳለው ባንኩ ብድር ወስደው መክፈል ባለመቻላቸው ንብረታቸው በጨረታ ሂደት ላይ ያሉ ደንበኞች ወረርሽኙ እልባት እስኪያገኝ ድረስ ለጊዜው የጨረታ ሂደቱ እንዲቆም መወሰኑን አብራረተዋል።

የብድር ማራዘሚያ የሚከፈለው የአገልግሎት ክፍያ በእነዚህ ብድሮች ላይ ተፈጻሚ እንደማይሆን መናገራቸውን የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.