Fana: At a Speed of Life!

የዜጎችን ሰላምና ደህንነት እንዲሁም የሀገርን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ብቸኛው መፍትሄ የህግ የበላይነትን ማስከበር መሆኑን መንግስት ገለፀ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 12፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የዜጎችን ሰላምና ደህንነት እንዲሁም የሀገርን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ብቸኛው መፍትሄ የህግ የበላይነትን ማስከበር መሆኑን መንግስት አስታወቀ።

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማምሻውን ባወጣው መግለጫ፥ በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የሚታየውን ህገወጥነትና የሰላም መደፍረስ እንዲሁም ስርዓት አልበኝነትን መንግስት እንዲቆጣጠር ህዝቡ በተደጋጋሚ በአንድ ድምፅ ሊባል በሚችል መልኩ ሲጠይቅ መቆየቱን አንስቷል።

ከሰሞኑ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም ክልሎች ውስጥ የፌደራልና የክልል የፀጥታ ኃይሎች እየወሰዱት ያለው ህግ የማስከበር እርምጃ የዚሁ አካል መሆኑን ነው ያስታወቀው።

በሁሉም ክልሎች እየተካሄደ በሚገኘው ኦፕሬሽን በርካታ ግለሰቦችና ቡድኖች ከነትጥቆቻቸዉ፣ ከዘረፉት ንብረትና ቀጣይ ሊፈፅሙ ያቀዷቸዉ ጥፋቶችን ካሰፈሩባቸው ሰነዶች ጋር በቁጥጥር ስር እንዲዉሉ እየተደረገ መሆኑንም የገለፀው መግለጫው፥ ጉዳያቸውም ተገቢውን ሂደት ጠብቆ እየተጣራ ለፍርድ እንዲቀርቡ እየተደረገ ይገኛል ብሏል።

መንግስት በሆደ ሰፊነት በተደጋጋሚ ጊዜ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ከቁብ ያልቆጠሩ ኃይሎችን መግታት የሚቻለው የህግ የበላይትን በማስከበር ብቻ ነው ያለው መግለጫው፥  ሁሉም ዜጋና የተለየ አመለካከት ያላቸው ወገኖችም መብትና ጥቅሞቻቸውን ማስከበር የሚችሉት የህግ የበላይነት ሲረጋገጥና ሰላም ሲሰፍን ብቻ መሆኑን አስታውቋል፡፡

የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦

የዜጎችን ሰላምና ደህንነት እንዲሁም የሃገርን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ብቸኛው መፍትሄ የህግ የበላይነትን ማስከበር ነው!
በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የሚታየውን ህገወጥነትና የሰላም መደፍረስ እንዲሁም ስርዓት አልበኝነትን መንግስት እንዲቆጣጠር መላ ህዝባችን በተደጋጋሚ በአንድ ድምፅ ሊባል በሚችል መልኩ ሲጠይቅ ቆይቷል፡፡ ቀደም ሲል ብሔራዊ የፀጥታ ም/ቤት እነዚህን ጉዳዮች በመገምገም አስፈላጊው እርምጃ መወሰድ እንዳለበት ማስታወቁም የሚታወስ ነው፡፡ ከሰሞኑ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም ክልሎች ውስጥ የፌደራልና የክልል የፀጥታ ኃይሎች እየወሰዱት ያለው ህግ የማስከበር እርምጃ የዚሁ አካል ነው፡፡
በኦሮሚያና በአጎራባች ክልሎች የሸኔ የሽብር ቡድን ከሌሎች የጥፋት ኃይሎች ጋር በመተባበር ህዝባችን ላይ እያደረሰ የነበረውን ጥቃት ለመቀልበስ መንግስት የተሳካ እርምጃ እየወሰደ ይገኛል፡፡ በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች በአልሸባብ የሽብር ኃይል ላይ እየተወሰደ የሚገኘውም እርምጃ ውጤታማ በሆነ መንገድ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ከሰሞኑ ደግሞ በአማራ ክልል በህገወጥ የጦር መሳሪያና ገንዘብ ዝውውር፤ በቡድን ተደራጅቶ ግለሰቦች ያፈሩትን ሃብትና ንብረት በመዝረፍና በማውደም ላይ የተሰማሩ፤ በነፍስ ግድያ የሚጠረጠሩ፣ አንዱን ህዝብ ከሌላው ጋር በማጋጨት ክልሉ እንዳይረጋጋ በሚያደርጉ ቡድኖች ላይ መጠነ ሰፊ እርምጃ እየተወሰደ ይገኛል፡፡ በአዲስ አበባና በዙሪያው ኦሮሚያ ከተሞች በቡድን ተደራጅተው በልዩ ልዩ የዝርፊያ ወንጀሎች ላይ የተሰማሩ፣ የጦር መሳሪያና የገንዘብ ዝውውር አቀባባይ በሆኑ ቡድኖችና ግለሰቦች፤ እንዲሁም በወያኔ ሰርጎ ገቦች ላይም መንግስት ቁርጠኛ እርምጃ እየወሰደ ይገኛል፡፡ በሁሉም ክልሎች እየተካሄደ በሚገኘው ኦፕሬሽን በርካታ ግለሰቦችና ቡድኖች ከነ ትጥቆቻቸዉ፤ ከዘረፉት ንብረትና ቀጣይ ሊፈፅሙ ያቀዷቸዉ ጥፋቶችን ካሰፈሩባቸው ሰነዶች ጋር በቁጥጥር ስር እንዲዉሉ እየተደረገ ነው። ጉዳያቸውም ተገቢውን ሂደት ጠብቆ እየተጣራ ለፍርድ እንዲቀርቡ እየተደረገ ይገኛል፡፡
መንግስት ህግና ስርዓትን በማስከበር የዜጎች ደህንነትና የሀገር ቀጣይነትን ለማረጋገጥ እየወሰደ ላለው እርምጃ መላው ህብረተሰብ ከፍተኛ ድጋፍ እየሰጠ ይገኛል፡፡ በሁሉም ክልሎች መላው ህዝባችን የጥፋት ሰንሰለቶቹን ከማጋለጥ ጀምሮ አጀንዳውን የሁከትና ብጥብጥ ማስፈፀሚያ ለማድረግ የሚጥሩ ኃይሎችን እየታገለ ይገኛል፡፡ በአንፃሩ የተለያዩ ስያሜዎችን በመስጠት የመንግስትን እርምጃ ለማጠልሸት የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች መኖራቸውን መንግስት አረጋግጧል፡፡ አሸባሪው ህወሃት እና ጀሌዎቹ መንግስት እየወሰደ ባለው እርምጃ ሁከትና ብጥብጥ ለመፍጠር የሚንቀሳቀሱ ህገወጥ ቡድኖችን በተለይም በአማራ ክልል የህግ የማስከበር ስራዎችን ለማደናቀፍ የሚሞከሩ ህገወጥ እንቅስቃሴዎችን ለማባባስ ከወዲሁ አጋርነታቸውን በይፋ እየገለፁ ነው፡፡ ይህ የሚያመለክተን እነዚህ ቡድኖች በተለይም በፋኖ ስም የሚነግዱ የዝርፊያ ቡድኖች በህዝባችን ላይ ከፍተኛ ክህደት የፈፀሙ ታሪካዊ የኢትዮጵያ ጠላቶች እና የተላላኪዎቻቸው ዓላማ ማስፈፀሚያ መሆናቸው ነው፡፡
መላው ህዝባችን ይህንን እኩይ ሴራ በመገንዘብ መንግስት እየወሰደ ያለውን እርምጃ በመደገፍ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ መንግስት ይጠይቃል፡፡ ለሃሰተኛ መረጃዎችና የጥፋት መልእክትን ለያዙ ወሬዎች ጆሮ ባለመስጠት የህግ የበላይነትን የማስከበሩን እርምጃ እንደ እስካሁኑ በሙሉ አቅሙ ማገዙን እንዲቀጥልም ጥሪውን ያቀርባል። መንግስት በበኩሉ በህገወጥ ተግባር ላይ በመሳተፍ፤ ሁከትና ብጥብጥ እንዲፈጠር ሆነ ብለው፤ አቅደዉ በሚሰሩ አካላትና ግለሰቦች እንዲሁም የሚዲያና የጋዜጠኝነት ካባ ደርበው ሁከትና ብጥብጥ እንዲፈጠር በሚንቀሳቀሱ አካላት ላይ የሚወሰደውን የማያዳግም እርምጃ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡

 

የዜጎች ሰላም፣ ደህንነትና የሀገር ቀጣይነት የሚረጋገጠው የህግ የበላይነት ሲከበር ብቻ ነው፡፡ በመላ ኢትዮጰያ የሚገኘው ዜጋ በሰላም ወጥቶ የመግባት መብቱ እንዲከበርና ደህንነቱ እንዲጠበቅ የህግ የበላይነትን ማስፈን ደግሞ ህዝብ ለመንግስት የሰጠው ሃላፊነት ነው። የዜጎች ነፃነትና ዲሞክራሲም መስፈን የሚችለዉ የትኛውም ጉልበት አለኝ የሚል አካል ከህግ በታች መሆኑ እስከተረጋገጠ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ነፃነትንና መብትን ከለላ በማድረግ የሚፈፀም የትኛውም አይነት እኩይ ተግባርን መንግስት አይታገስም፡፡ መንግስት በሆደ ሰፊነት በተደጋጋሚ ጊዜ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ከቁብ ያልቆጠሩ ኃይሎችን መግታት የሚቻለው የህግ የበላይትን በማስከበር ብቻ ነው፡፡ ሁሉም ዜጋና የተለየ አመለካከት ያላቸው ወገኖችም መብትና ጥቅሞቻቸዉን ማስከበር የሚችሉት የህግ የበላይነት ሲረጋገጥና ሰላም ሲሰፍን ብቻ ነው፡፡

የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት!!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.