Fana: At a Speed of Life!

የጁንታው ቡድን ልዩ ሃይል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የጦር መሳሪያ በማስቀመጥ ህብረተሰቡን ያስቆጣ ተግባር ፈጽሟል – መከላከያ ሰራዊት

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 19 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የጁንታው ቡድን ልዩ ሃይል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የጦር መሳሪያ በማስቀመጥ ህብረተሰቡን ያስቆጣ ተግባር መፈጸሙን የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት አስታወቀ፡፡

“በራያ ግንባር የተሰለፈው የመከላከያ ሰራዊት በሚያከናውነው የህግ ማስከበር ተልዕኮ ተደጋጋሚ ሽንፈቶችን እየተጋተ የሚገኘው የጁንታው ቡድን የማይደፈረውን ነገር ፈጽሟል” ብሏል።

በዚህም በአዲ ምስኖ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዛት ያላቸው ጥይቶችን በማከማቸት የአካባቢውን ህብረተሰብ ያስቆጣ አረመኔያዊ ተግባር መፈጸሙንም ሰራዊቱ በፌስ ቡክ ገጹ ባወጣው መረጃ አስታውቋል ።

አቶ በሀይሉ በርኸ ” ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የመድፍ ጥይት እና ቢ ኤም መሳሪያ አምጥተው አስቀመጡ ለምን ስንላቸው ቤተክርስቲያኑ አይመታባችሁም ከተመታም የጥይት ሳጥን እንሰጣችሁና እሱን ሸጣችሁ ታስጠግኑታላችሁ አሉን ” ብለዋል ።

አቶ በሀይሉ “ቤተ ክርስቲያኑ ፈርሷል ውስጡ ያለው ፅላትም ይኑር አይኑር የምናውቀው ነገር የለም ፥ ወያኔ ለሃይማኖት እኩልነት እቆማለሁ ሲል የነበረ ድርጅት ዛሬ ግን ስጋወደሙ የምንቀበልበትን የእምነት ቦታ አርክሶብናል” ሲሉ በሃዘንና በቁጭት ስሜታቸውን እንዳጋሯቸውም ነው ያስታወቀው።

በየትኛውም ፖለቲካዊ እይታ ህዝብን ያልያዘ ሃይል የድል ባለቤት ሊሆን አይችልም ያለው ሰራዊቱ፥ ከሞቱ መቃብር አፋፍ ላይ የሆነው ትህነግ ግን በራሱ ልክ በተሰፋው የሴራ ፖለቲካ ተተብትቦ በሰው ህሊና ሊፈፀሙ አይደለም ሊታሰቡ የማይችሉ ተግባራትን ከመፈፀም አልቦዘነምም ነው ያለው።

ለሁሉም በመላው ህዝብ ድጋፍ በጀግናው መከላከያ ሰራዊት ጀግንነት ዘራፊውና ከሃዲው ቡድን ያለችው የተስፋ ጭላንጭል ተሟጣ የመኖር ጀንበሩ ልትጠልቅ አጭር እድሜ ብቻ ቀርተውታልም ብሏል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.