Fana: At a Speed of Life!

የገንዘብ ሚኒስቴር ለትግራይ ወረዳ፣ ከተማና ቀበሌ የሚሰጠውን የድጎማ በጀት የሚተላለፍበትን አሰራር አዘጋጅቶ አጠናቀቀ

አዲስ አበባ ፣ ጥቅምት 12 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የገንዘብ ሚኒስቴር ለትግራይ ወረዳ፣ ከተማና ቀበሌ የሚሰጠውን የድጎማ በጀት የሚተላለፍበትን አሰራር አዘጋጅቶ ማጠናቀቁን ገለጸ።

የፌዴሬሽን ምክር ቤት ነሃሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባና በወሰነው ውሳኔ መሰረት እንዲሁም መስከረም 26 ቀን 2013 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የትግራይ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ኢ-ህገ መንግስታዊ ምርጫን በማድረግ፣ አዲስ የክልል ምክር ቤትና ከፍተኛ የህግ አስፈጻሚ አካል በመመስረቱ ከፌደራል መንግስት ጋር ያለው ግንኙነት ከክልሉ ወረዳ ከተማና ቀበሌ መዋቅሮች ጋር እንዲሆን በፌደራል መንግስት መወሰኑ ለአሰራሩ መዘጋጀት ምክንያት ሆኗል ተብሏል።

በዚህም መሰረት የገንዘብ ሚኒስቴር ለትግራይ ወረዳ ከተማና ቀበሌ የሚሰጠውን የድጎማ በጀት የሚተላለፍበትን ዝርዝር ስራ የገንዘብ ሚኒስቴር አዘጋጅቷል።

ሚኒስቴሩ ያዘጋጀው ዝርዝር የበጀት ማስተላለፊያ አሰራርም ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ ከጸደቀ በኋላ ተግባራዊነቱ እንደሚፈጸም ታውቋል።

ራሱን የትግራይ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ነኝ ብሎ ለሚጠራው አካል የሚተላለፍ በጀት እንደማይኖርም ሚኒስቴሩ አስታውቋል።

ሚኒስቴሩ ከወረዳ ከተማና ቀበሌ የበጀት ድጎማ አፈጻጸም ጋር ለሚነሱ ጥያቄዎች የድጎማ በጀት የሚተላለፍበት አሰራር ዝርዝር በምክር ቤቱ ከጸደቀ በኋላ እንደሚገለጽም የገንዘብ ሚኒስቴር የኮሙዩኒኬሽንና ኢንፎርሜሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ አቶ ሃጂ ኢብሳ ተናግረዋል።

በተስፋዬ ከበደ

#FBC
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.