Fana: At a Speed of Life!

የፌደራል ፍርድ ቤቶች በመስከረም ወር በከፊል ዝግ ሆነው ይቆያሉ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 3፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በመስከረም ወር 2013 ዓ.ም በከፊል ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አስታወቀ፡፡

ይህም ፍርድ ቤቶች የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ለመከላከል ከመጋቢት 10 – እስከ ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም በከፊል ዝግ ሆነው ከቆዩብ ሁኔታ ለመውጣትና ተቋርጦው የነበሩት አገልግሎቶችን ደረጃ በደረጃ ለማስጀመር ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም ባወጣው መመሪያ መሰረት ዳኞች በመስከረም ወር እረፍት አንዲያደርጉ በመወሰኑ ነው ተብሏል፡፡

ዳኞች ዓመታዊ እረፍታቸውን በነሃሴ እና በመስከረም ወር የሚወስዱ በመሆኑ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች አስቸኳይነት ያላቸውን ጉዳዮች ብቻ በተረኛ ችሎቶች በማስተናገድ በከፊል ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ ማድረግ የተለመደ አሰራር መሆኑን ያስታወሰው ጠቅላይ ፍርድ ቤት፤ በዚህ ዓመት ዳኞች አጭር የእረፍት ጊዜ እንደሚኖራቸው ገልጿል፡፡

ፍርድ ቤቶቹ በከፊል ዝግ ሆነው በሚቆዩባቸው የመስከረም ወር 20 የስራ ቀናት አስቸኳይና ጊዜ የማይሰጡ ከዜጎች መሰረታዊ መብቶች እንዲሁም ከሀገር ሰላምና ፀጥታ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ጉዳዮች እንደሚመለከቱ ተገልጿል፡፡

በዚህም እንደ የጊዜ ቀጠሮ፣ የዋስትናና የዕግድ ጥያቄዎች፣ የመያዣና የብርበራ ትዕዛዞች፣ በተፋጠነ ስነ-ስርዓት የሚታዩ የእጅ ከፍንጅ ወንጀሎች እንዲሁም ከቤተሰብና ከሕፃናት ቀለብና አስተዳደግ ጋር የተያያዙ አጣዳፊ መሰረታዊ ጉዳዮች በተረኛ ችሎቶች የሚስተናገዱ መሆኑን ፌዴራል ከጠቅላይ ፍርድ ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.