Fana: At a Speed of Life!

ዴክሳሜታሰን መድሃኒት በኮሮና ቫይረስ በፅኑ የታመሙትን ሰዎች ህይወት እንደሚታደግ የብሪታንያ ተመራማሪዎች ገለፁ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 9፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በአነስተኛ ዋጋ በስፋት የሚገኘው “ዴክሳሜታሰን” የተባለው መድሃኒት በኮሮና ቫይረስ በፅኑ የታመሙትን ሰዎች ህይወት ለመታደግ እንደሚረዳ የብሪታንያ ተመራማሪዎች ገለፁ።

እንደተመራማሪዎቹ ገለፃ በመድሃኒቱ በአነስተኛ ዶዝ በሚሰጠው የስቴሮይድ ህክምና የኮሮና ቫይረስን በመዋጋት ሂደት ከፍተኛ ውጤት የሚያመጣ ነው።

መድሃኒቱ በተለይም በመተንፈሻ መሳሪያዎች (ቬንትሌተር) እና ኦክሲጅን ድጋፍ የሚተነፍሱትን ታማሚዎች የመሞት እድልን የሚቀንስ መሆኑንም አስታውቀዋል።

እንደ ተመራማሪዎቹ ገለፃ መድሃኒቱ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽን በብሪታኒያ እንደገባ ጥቅም ላይ መዋል ቢጀምር እስከ 5 ሺህ የሚደርሱ ሰዎችን ህይወት መታደግ ይቻል ነበረ።

“ዴክሳሜታሰን” የተባለው መድሃኒት ዋጋም አነስተኛ በመሆኑ በተለይም ከፍተኛ የኮሮና ቫይረስ ታማሚዎችን ለያዙ በዝትቀኛ የገቢ ደረጃ ላይ ላሉ ሀገራት ጠቃሚ መሆኑንም አስታውቅዋል።

በኮሮና ቫይረስ ከተያዙ 20 ሰዎች ውስጥ 19 በቶሎ የሚያገግሙ መሆኑን ያስታወቁት ተመራማሪዎቹ፥ በፀና ታመው ሆስፒታል ከሚገቡት መካከል ውስጥ ግን የተወሰኑት እንደ ቬንትሌተር እና ኦክሲጅን አጋዥ የመተንፈሻ መሳሪያዎች ያስፈልጋቸዋል ይላሉ።

ታዲያ “ዴክሳሜታሰን” የተባለው መድሃኒትም በአጋዥ የመተንፈሻ መሳሪያዎች ለሚያስፈልጋቸው ታማሚዎች ነው ጥቅም ላይ የሚውለውም ብለዋል።

በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ቡድን በመድሃኒቱ ላይ በተደረገው ጥናትም በሆስፒታል ውስጥ ለሚገኙ 2 ሺህ ሰዎች “ዴክሳሜታሰን” እንዲሰጥ በማድረግ መድሃኒቱን ካልወሰዱት 4 ሺህ ሰዎች ጋር በማነፃፀር ተመልክቷል።

በዚህም በመተንፈሻ መሳሪያዎች (ቬንትሌተር) ድጋፍ ላይ ባሉ ታማሚዎችላይ የሚከሰት ሞትን ከ40 እስከ 28 በመቶ ቀንሷል ያሉ ሲሆን፥ በኦክሲጅን ታግዘው በሚተነፍሱ ታማሚዎች ላይ የሚከሰትን ሞትን ደግሞ ከ25 እስከ 20 በመቶ መቀነሱን አስታውቅዋል።

የጥናት ቡድኑ መሪ ፕሮፌሰር ፒተር ሆርቢ ፥ እስካሁን ከተደረጉ ሙከራዎች በኮሮና ቫይረስ የሚከሰት ሞትን በመቀነስ ረገድ “ዴክሳሜታሰን” መድሃኒት የመጀመሪያው መሆኑን እና በኮቪድ 19 ላይ በሚደረገው ምርምርም ትልቅ ውጤት መሆኑን ተናግረዋል።

በጥናቱ ላይ የተሳተፉት ፐሮፌሰር ማርቲን ላንድረይ በበኩላቸው፥ መድሃኒቱ በዓለም ዙሪያ የሚገኝ መሆኑ እና ዋጋውን አነስተኛ መሆኑ በፅኑ የታመሙ ሰዎችን ህይወት በመታደግ ረገድ ከፍተኛ ጥቅም አለው ብለዋል።

ሆስፒታሎች በኮቪድ 19 በጽኑ ለተመሙ ታካሚዎቻቸው መድሃኒቱን እንዲሰጡ እናበረታታለን ያሉት ፐሮፌሰር ማርቲን ላንድረይ፥ ሆኖም ግን መድሃኒቱ በጽኑ ለታመሙት ብቻ የሚያገለግል በመሆኑ ሰዎች በራሳቸው ፍቃድ ገዝተው ሊጠቀሙት አይገባም ሲሉም አሳስበዋል።

ምንጭ፦ ቢቢሲ

#FBC

የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.