Fana: At a Speed of Life!

ጠላቶቻችንን በብሩህ ተስፋችንም ጭምር ፊታቸው ጠቁሯል ₋ ኢዜማ

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 14 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)አበውስጥና በውጪ ጠላቶች የተደቀነባትን አደጋ በጀግኖች ልጆቿ መራር ትግልና መሰዋዓትነት በድል እንደመትወጣ ሙሉ እምነት አለው፡፡
ጠላቶቻችንን በደማቅ የአሸናፊነት ታሪካችን ብቻ ሳይሆን በብሩህ ተስፋችንም ጭምር ፊታቸው ጠቁሯል፡፡
በዚህም ዛሬም እንደ አራዊት እርስ በእርስ ሊያናክሱንና ሊያጠፋፉን፤ ማንነታችንን እና ክብራችንን ሊያዋርዱ ጦርነት ከፍተውብናል፡፡
ኢትዮጵያውያን በአሸናፊነት የምንቋጨው ጦርነት ላይ ብንሆንም ጦርነቱን በአጠረ ግዜ አለመጨረስ የሚያስከትለብን ፈተና ከባድ ይሆናል፡፡
የተራዘመ ጦርነት እንደ እሳት ነበልባል ሀገራችንን እና ህዝቦቿን ይበላል፡፡
ለውጭ ጠላቶቻችንን የበረታ ጫና ተጨማሪ ዕድል ይሰጣል፡፡
ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳቱም እጅግ የበዛ ነው፡፡
ስለሆነም መላው ኢትዮጰያዊያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች የህልውና ጦርነቱን በአጭር ግዜ ግቡን እንዲመታና የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ባረጋገጠ መልኩ እንዲቋጭ ዛሬ ነገ ሳትሉ የሚጠበቅባችሁን የዜግነት ግዴታ እንደምትወጡ አንጠራጠርም፡፡
የዜግነት ግዴታችንን ስንወጣ የሀገራችን ፓለቲካ በብዙ ውስብስብ ችግሮች ውስጥ የሚገኝ መሆኑን ዘንግተን አይደለም፡፡
ያለን የፖለቲካ አመለካከት ልዮነቶች እንደተጠበቁ ሆነው በተለይ በእንዲህ ያለ ግዜ ለሀገር ህልውና በጋራ መቆሙ ምርጫ የሌለው ግዴታችን በመሆኑም ጭምር ነው፡፡
ሀገሬን እና ህዝቤን እወዳለሁ የሚሉ ሁሉ በተግባር የሚፈተኑበት ግዜው አሁን ነው፡፡
ሲተቹና አስተያያት ሲሰጡ የነበሩ ሁሉ የተናገሩትን ፈፅመው ሀቀኞች መሆናቸውን የሚያረጋግጡበት ቀን ደርሷል፡፡
ጥሬው ከብስሉ የሚለይበት ከንግግር ያለፈ ተጨባጭ ሥራ ሰርተን በታሪክ ፊት በእውነት የምንመዘንበት የታሪክ አጋጣሚ ከእጃችን ላይ ነው፡፡
ኢዜማ ለመላው የፓርቲው አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና ለመላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን በጋራ ሊያጠፋን የመጣውን ኃይል በህብረት ለመደምሰስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
በመላው ኢትዮጵያ የምትገኙ አባላትና ደጋፊዎች ይህን ዘመቻ ሊያጠናከርና ሊደገፍ በሚችል አደረጃጀት ውስጥ በመቀላቀል፤ በገንዘብና በጉልበት ተግባራዊ ድጋፍ በማደረግ እውነተኛ ደጀን በመሆን፤ እንዲሁም የአካባቢያችንን ፀጥታ በንቃት በመጠበቅና አጥፊዎችን በአግባቡ ለሕግ በማቅረብ ብሎም ከተሳሳተ ፐሮፖጋንዳ ራሳችንን በመጠበቅ ይህን የፈተና ወቅት በፅናት እንድንወጣ አደራ እንላለን፡፡
በዚህ አሰቸጋሪ ወቅት ከፊት ሆነው እየተዋደቁ ያሉ ጀግኖችን ሁሉ በርቱ ታሪካችን ደማቅ ድላችንም አንፀባራቂ እንደሚሆን አትጠራጠሩ እያልን ወደ ግንባር የዘመቱት ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ ለጉዳዩ ክብደት የሰጡት ትኩረት ተገቢ ነው እያልን በዚህ ሂደት ውስጥ የጸጥታውን መዋቅር በአንድ ወጥ አመራር አሰልፈው የሀገራችንን ድል ያፋጥኑታል ብለን እንተማመናለን፡፡
ስለዚህም ወጥ በሆነ የዕዝ ሰንሰለትና በተጠና ሀገር አቀፍ የውጊያ ስልት ሃገራችንን ለመጠበቅ ቆራጦች መሆናችንን እንገልጻለን፡፡
ኢትዮጵያውያን ፣ ትውልደ ኢትዮጵያውን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች በዓለም አደባባይ ተገኝታችሁ ለምትወዷት ሀገራችሁ ሉዓላዊነት እያደረጋችሁ ላለው እጅግ የሚያስመካ ተግባር ኢዜማ ከፍ ያለ ክብር አለው፡፡
አንዳንድ የውጪ ሀገር መንግስታት እና ተቋማት ኢትዮጵያዊያን የሀገራችንን ህልውና ላይ የተጋረጠውን አደጋ ለመመከት እያደረግን ያለው ተጋድሎ ላይ እያሳረፉ ያሉትን ያልተገባ ጫና እንዲያቆሙ ድምጻችሁን አሰምታችኋል ፤ ድጋፋችሁን የሚሹ ወገኖቻችሁንም ሳትሰስቱ እየረዳችሁ ነው።
ካለንበት ውስብስብ ችግር አንፃር ሲታይ እናት ሀገራችሁ ከመቼውም ጊዜ በላይ የእናንተን አቅም እና ድጋፍ አሁንም ትሻለች። ያለእናንተ አስተዋፅዖ የተሟላ ድል ሊገኝ እንደማይችል በተግባር ተረድተናል፡፡
ስለሆነም የምዕራባውያንን የተዛባ አመለካከት በማጥራት እንዲሁም ሊፈጠር የሚችለውን የኢኮኖሚ ጫና ለመቅረፍ በሚያስችል ደረጃ የተደራጀ እና ወጥነት ያለው ድጋፍ ለማድረግ ከወትሮው በላቀ ሁኔታ በያላችሁበት የዓለም ጥግ እራሳችሁን እንድታዘጋጁ አደራ እንላለን፡፡
በመጨረሻም ከልዩነቶቻችን፣ አለመግባባቶቻችን እና የጎደሉን ነገሮች በፊት ኢትዮጵያ ሃገራችን ትቀድማለች፡፡ በተለይ የፖለቲካ ልዩነቶችን ለመፍታት የሀገራችን ህልውና ቀዳሚ ነው።
የመጣብንን የጋራ ጠላት በጋራ መክተን የሀገረ መንግስቱን ቀጣይነት ካረጋገጥን በኋላ ልዩነቶቻችንን ለመፍታት እና ቅሬታዎቻችንን ለማከም በጠረጴዛው ዙሪያ እንቀመጣለን።
በዛም ወቅት ሀገራችንን የመፍረስ ስጋት ጫፍ ላይ ያደረሳት የፖለቲካ ስርዓት እና አካሄድ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዳይመለስ መስራት ሀላፊነታችን ይሆናል፡፡
አሁን ላይ ከምንም ምድራዊ ጉዳይ በላይ ቅድሚያ የምንሰጠው ሃገራችንን ማዳን፣ ኢትዮጵያችንን መጠበቅ ነው! ይህንንም ስናደርግ እንደ ሀገር አብሮ መኖራችንን በማያቆሽሽ እና የወደፊት አብሮነታችንን በማይጎዳ ሁኔታ እንዲሆን አሁንም አበክረን እናሳስባለን፡፡
አሁን ያለንበት ወቅት ሁሉን አቀፍ አርበኝነትን የሚጠይቅ መሆኑን ግምት ውስጥ በመክተት የኢዜማ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ አባላት እና ደጋፊዎቹ ግንባር ድረስ በመዝመት፣ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት በመስጠት እና ሌሎችንም ተግባራት በመከወን የሀገርን ህልውና የማረጋገጥ ስራ ለመስራት ውሳኔን አስተላልፏል፡፡
አካባቢዎን ይጠብቁ!
ወደ ግንባር ይዝመቱ!
መከላከያን ይደግፉ!
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.