Fana: At a Speed of Life!

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ወለጋ ብርቅዬ የማይጠገብ የፍቅርና የልማት አካባቢ መሆኑን ገለጹ

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 7፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የደምቢዶሎ- ሙጊ- ዶላ አስፓልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታን አስጀመሩ።

ግንባታውን የመስጀመር ስነስርአት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፥ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፥ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፥ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰመስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ እና ሌሎች የስራ ሀላፊዎች በደምቢዶሎ ከተማ በተገኙበት ተከናውኗል።

መንገዱ 50.9 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን በፌዴራል መንግስት ወጪ በ1.6 ቢሊየን ብር ይካሄዳል።

ግንባታውን በሶስት አመት ተኩል ለማጠናቀቅ ኮንትራት የወሰደው የቻይናው ሬይልዌይ ሰቨንስ ግሩፕ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በመድረኩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ምዕራብ ኢትዮጵያ ብርቅዬ የማይጠገብ የፍቅርና የልማት አካባቢ መሆኑን ገልጸዋል።

ይህንን የማውቀው በወሬ ሳይሆን በተጨባጭ ኖሬበት ነው ብለዋል።

ወለጋ ለኦሮሞ ህዝብና ለኢትዮጵያ ነጻነትና ህልውና ተምሳሌት ነው ሲሉእ ተናግረዋል።

አብዲሳ አጋ ለኢትዮጵያ አንድነት ዋጋ የከፈለ በአካባቢው የተወለደ ጀግና ዘላለም ታሪክ የሚያስታውሰው መሆኑንም ተናግረዋል።

በተጨማሪም ቄስ ጉዲና ቱምሳ የኢትዮጵያው ማርቲን ሉተር ነው ሲሉ ገልጸዋል።

አካባቢው የሌሎች ጀግኖች መፈጠሪያ መሆኑንም አስታውሰዋል።

ወለጋ የነጻነት ታጋይ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በመሰረተልማት ችግር ግን ሳይጠቀም እና የሚገባውን የልማት ድርሻ ሳይወጣ ቆይቷል ነው ያሉት።

በአካባቢው የሚገነቡ ፕሮጀክቶች ወለጋን ከአጎራባች የሀገሪቱ ክልሎችና ሀገራት ጋር ለማገናኘት የታሰበ ነው ብለዋል።

አካባቢው ተዘንግቶ የቆየ በመሆኑ ልዩ ትኩረት ስለሚሻ በትኩረት እየሰራን እንገኛለን ነው ያሉት።

ነዋሪው የአካባቢውን ሰላምና ጸጥታ በመጠበቅ ልማት እንዲፋጠን የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ወለጋ የታዋቂዎች እና የሀገር ባለውለታ አካባቢ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

የሰላምና ጸጥታ ችግሮችን ችላ ሳንልና ሳንዘናጋ ለህዝቡ ተጠቃሚነት እና አንድነት እንሰራለን ብለዋል።

ለመለወጥና ለሀገር አንድነት ግንባታ ጊዜው አሁን ነው ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ርዕሰመስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በበኩላቸው የረዥም ዘመናት የህዝቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ የሚደረገው ስራ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።

ከዚህ በፊት በአንድ እጃችን ብቻ የልማት ስራ እንሰራ ነበር፥ አሁን ግን በሙሉ ሀይል እና በሁለት እጅ ወደ ልማት ፊታችንን አዙረናል ብለዋል።

መንግስት ቅናተኞችን እና ተላላኪዎቻቸውን ወደ መስመር እያስገባ ይገኛል ነው ያሉት አቶ ሽመልስ አብዲሳ።

የአደናቃፊዎች ምኞት እንዳይሳካ መንግስትና ህዝቡ በትብብር ይሰራል ብለዋል።

ከዚህ ቀደም መሰረተ ድንጋይ በመኪና በመጫን በየቦታው ይጣል ነበር፥ አሁን ግን በጀት መድበን የምንጨርሰውን ፕሮጀክት በማስጀመር እና ሰርተን በማስመረቅ ለህዝቡ ተስፋና ልማትን እናበስራለን ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት መተግበሪያን https://play.google.com/store/apps/details… በስልክዎ በመጫን ቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት፣ ኤፍኤም 98.1 እና ብሄራዊ ሬዲዮን ይከታተሉ፡፡ ቪዲዮዎችንም ይመልከቱ፡፡
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.