Fana: At a Speed of Life!

ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ከዓለም አቀፍ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ፕሬዚዳንት ጋር ተወያዩ

አዲስ አበባ ፣ ጥር 6 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ከዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ፕሬዚዳንት ፒተር ማውራ ጋር ተወያይተዋል።

በውይይታቸውም የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ በኢትዮጵያ በሚያከናውናቸው ተግባራት ዙሪያ መክረዋል።

ዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ በኢትዮጵያ በጎሳ ግጭት እና አለመረጋጋት ለተጎዱ ዜጎች የሚያደርገውን ሰብዓዊ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ፕሬዚዳንት ፒተር ማውራ ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት እያደረጉ የሚገኙት ፒተር ማውራ ከሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሃመድ ኦማር ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸው የሚታወስ ነው፡፡

በክልሉ ቆይታቸውም በጅግጅጋ ከተማ በዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ድጋፍ የሚደረግለትን የአካል ጉዳተኞች መልሶ ማቋቋሚያ ማዕከል ጎብኝተዋል።

በተጨማሪም በኦሮሚያ ክልል ጭናቅሰን ወረዳ በዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ ድጋፍ የተከናወኑ መሰረታዊ ጤና ጣቢያ ስራዎች መመልከታቸውን ከዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ኮሚቴ በኢትዮጵያ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.