Fana: At a Speed of Life!

ህግ የማስከበር ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኦሮሚያ ክልል መንግስት አስታወቀ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 23፣2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ህግ የማስከበር ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል እና የሚጠሩ ሰላማዊ ሰልፎች ተቀባይነት የሌላቸው መሆኑን የኦሮሚያ ክልል መንግስት አስታወቀ።
 
የክልሉ የሰላምና ደህንነት ቢሮ ዛሬ በሰጠው መግለጫ በተለያዩ የክልሉ አካባቢዎች ለውጡ ከግብ እንዳይደርስ ፣ ልማት እንዲደናቀፍና ፣ ህዝቡ ሰላም እንዲያጣ የሚሰሩ አካላት መኖራቸውን ገልጿል።
 
የቢሮው ሃላፊ አቶ ጅብሪል መሀመድ እንዳሉት ይሄው ሃይል በአንድ በኩል ትጥቅ በሌላ በኩል ህጋዊ አካሄድን እየተከተለ ሀገር እንድትሸበር እና ህዝቡ በመንግስት እምነት እንዲያጣ ሀሰተኛ መረጃን በማሰራጨት ላይ ይገኛል።
ለበርካታ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ለፁሃን ዜጎች ሞት ምክንያት ሆኖ ሳለ፤ መንግስት የፈፀመው በማስመሰል መገናኛ ብዙሃንን በመጠቀም የሃሰት ወሬ እያሰራጩ መሆኑም በመግለጫው ተገልጿል።
 
መገናኛ ብዙሃኑም ለሽብር የሚያነሳሱ እና ሰላምን ለማወክ እየተንቀሳቀሱ በመሆኑ መንግስት ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ይገደዳል ብለዋል።
 
አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባወጣው ሪፓርትም በሂደቱ የተሳተፉት መረጃ ሰጭዎች የኦነግ ሸኔ አባላት በመሆናቸው ፤ መረጃው በኦነግ ሸኔ አባላት የተፈፀሙ ጥሰቶችን ያላካተቱ እና በጉዳዩ የመንግስትን ሃሳብ ያላካተተ በመሆኑ ተቀባይነት የሌለው ነው ብሏል ቢሮው በመግለጫው።
 
አሁንም ለውጡን በማይፈልጉ አካላት ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተቃረነ መልኩ በሃሰተኛ መረጃ ድብቅ አጀንዳ ባላቸው አካላት ሰልፍ እየተጠራ መሆኑም ተደርሶበታል ተብሏል።
 
የዚህ ሰልፍ መነሻዎችም የመንግስትን ስልጣን ለመያዝ ወይንም ለመጋራት፣ የሽግግር መንግስት የማቋቋም ፍላጎት እንዲሁም በለውጡ ስልጣናቸውን ያጡ ጥግ የያዙ የህውሓት ባለስልጣናት እጅ ናቸው ብለዋል።
 
ሰልፉም ሀገሪቷ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ላይ መሆኗ፣ የህዳሴ ግድቡ ጉዳይ ከመቼውም ጊዜ በላይ በግብፅ ፍላጎት በባንዳዎች ሴራ አደጋ ላይ በመውደቁ፣ ከስልጣናቸው የተገፉ የቀድሞ ባለስልጣናት ብጥብጥ በመፍጠር እንደገና የመመለስ ፍላጎት ያላቸው እና የክልሉ መንግስት ያዳከመው የሽምቅ ተዋጊ እንደገና ለማንሰራርት ሁከት የመፈጠር ፍላጎት ያለው በመሆኑ በምንም መልኩ መካሄድ የማይችል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል ነው የተባለው፡፡
 
ህዝቡም እንደትላንቱ ሁሉ ለውጡን እንዲጠብቅ የፀጥታ መዋቅሩም ህግ የማስከበር ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።
 
በሃብታሙ ተክለስላሴ
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዘናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.