Fana: At a Speed of Life!

ሕወሓት ስልጣን ካጣ በኋላ ‘የጸጥታ ኃይል መምሪያ’ የሚል ዘርፍ አደራጅቶ ለሽብር ሲንቀሳቀስ ቆይቷል – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 2 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራት (ሕወሓት) በማዕከላዊ መንግስቱ ያለውን ስልጣን ካጣ በኋላ ወደ ትግራይ ክልል በመሄድ 2011 ዓ.ም ‘የጸጥታ ኃይል መምሪያ’ የሚል ዘርፍ አድራጅቶ ለሽብር ተግባር ሲዘጋጅ መቆየቱን የፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ገለጸ።

የፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ‘ሕወሓት እና ሽኔ’ ሽብርተኛ ያስባላቸውን ምክንያትና በአክሱም ከተማ ስለተፈጸመው ግድያ መግለጫ ሰጥቷል።

ባለፈው ሚያዚያ 28 ቀን ሁለቱ ድርጅቶች የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባቀረበው የውሳኔ ሃሳብ መሰረት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሽብርተኝነት መሰየሙ ይታወቃል።

መግለጫውን የሰጡት ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ ፍቃዱ ጸጋ ሁለቱ ድርጅቶች ሽብርተኛ ስለተባሉበት ሁኔታ ዛሬ ዝርዝር መግለጫ ሰጥተዋል።

“በዋናነትም ሁለቱ ድርጅቶች ሽብርተኛ የተባሉት ሰላማዊ ሕዝብን ከጥቃት ለመከላከል፣ የሕግ ማስከበር ስራውም እንዲጠናከርና ተባባሪዎቹን ለመቆጣጠር እንዲረዳ ነው” ብለዋል።

ሁለቱ ድርጅቶች በሽብርተኝነት ሕጉ መሰረት ሽብርን ዓላማ አድርገው የሚንቀሳቀሱ በመሆኑ፣ ድርጊታቸው የሽብር መገለጫ በመሆኑና የድርጅቶቹ ውሳኔ ሰጪ አካላት ሽብርተኝነትን በመቀበላቸው ነው ይላሉ።

በተለይ ደግሞ ሕወሓት ከስልጣን ሲወገድ ጀምሮ የተለያዩ ችግሮችን ሲፈጥር ቢቆይም ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ የተጠናከረ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

“በዚሁ መሰረት የጸጥታ ኃይል መምሪያ የሚል ዘርፍ በማደራጀት፤ መምሪያውንም ከመከላከያ የወጡ መኮንኖች እንዲመሩት አድርጓል” ይላሉ አቶ ፍቃዱ።

ይህንንም በማድረግ ከሚሊሻ ጀምሮ ለሁሉም የጸጥታ አካላት ሰፋፊ ስልጠናዎችን ሲሰጥ መቆየቱንም አንስተዋል።

ለአብነትም ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ከ37 ሺህ በላይ ሚሊሻ ማሰልጠኑን ገልጸዋል።

በቀደመው ጊዜ በዓመት ከ500 በላይ ልዩ ኃይል የማያሰለጥነው ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ግን በዓመት 5 ሺህ ልዩ ኃይሎችን ሲያሰለጥን መቆየቱንም ነው ያስታወሱት።

የክልሉን ሕዝብ በጦርነት ለማሳተፍም ከአርሶ አደር እስከ መንግስት ሠራተኛ ሰፋፊ ስልጠናዎችን ሲሰጥ መቆየቱንም ነው ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ የተናገሩት።

በተጨማሪም ህወሓት ሕገ ወጥ ምርጫ ማድረግ፣ በሦስት ወር ውስጥ የፌዴራል መንግስቱን መቆጣጠር የሚያስችል እቅድ ማውጣትና ግጭቶችን በገንዘብ ሲደገፍ መቆየቱ ተረጋግጧል ብለዋል።

“በዚህም በአፋር፣ በአማራ፣ በጋምቤላና በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልሎች ግጭቶች እንዲባበሱ ማድረጉና ሌሎች የድርጅቱ ተግባራት በሽብር የሚያሰይሙት ናችው” ነው ያሉት።

ይህ ብቻ ሳይሆን ጥቅምት 19 ቀን ‘ቀድሞ ማጥቃት’ በሚል ዝግጅት ጀምሮ ጥቅምት 24 የሰሜን እዝ አባላት ላይ ጥቃት በመሰንዘር የአገር መከላከያ ሠራዊቱን ማዋረዱም ሌለኛው ድርጅቱን ሽብርተኛ ያስባለ ተግባር ነው ብለዋል።

በተመሳሳይ ‘ሸኔ’ የተባለው ድርጅትም በምዕራብ ኦሮሚያና በደቡብ ኦሮሚያ ‘አባ ቶርቤ’ የተባለ ቡድን በማደረጀት የጸጥታ አካላትና አመራሮችን ሲገድል ቆይቷል ብለዋል።

ሸኔ የተባለው ድርጅት ንጹሃን ዜጎችን ከመግደል ባለፈ የመንግስት መዋቅርን የማፍረስ ድርጊት ሲፈጽም ቆይቷል ይላሉ ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ።

እሳቸው እንዳሉት ቡድኑ በ2013 ዓ.ም ብቻ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ 463 ሰዎች ላይ ጉዳት ያደረሰ ሲሆን ከነዚህም መካከል 112 ፖሊስ፣ 57 ሚሊሻ እና 18 በተለያዩ ደረጃ ያሉ አመራሮችን ገድሏል።

“በተጨማሪም በአክሱም ከተማ ስለተደረገው ግድያም ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በሁለት መንገድ ወንጀሉን እየመረመረ ይገኛል” ነው ያሉት።

ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ፍቃዱ በክልሉ በሴቶች መደፈር ጋር ተያይዞም የክልሉ ፍትህ ቢሮ ምርመራ እየተደረገ መሆኑንም ጨምረው ገልዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.