Fana: At a Speed of Life!

መከላከያ ሠራዊት ለትግራይ ወጣቶች እና ሚሊሻ አባላት ጥሪ አቀረበ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 5፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሀገር መከላከያ ሠራዊት የትግራይ ክልል ወጣቶች እና ሚሊሻ አባላት እጃቸውን በሰላም ለመንግስት እንዲሰጡ ጥሪ አቀረበ፡፡
የሀገር መከላከያ ሠራዊትጉዳዩን አስመልክቶ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ÷የጁንታው ጥቂት መሪዎች ባላቸው ስግብግብ የስልጣን ፍላጎትና ከህግ ተጠያቂነት ለመዳን ሲሉ የትግራይን ህዝብ ለጦርነት በመማገድ ከንቱ መስዋዕትነት እያስከፈሉት መሆኑ ን አንስቷል፡፡
ህወሓት ከአጎራባች ክልሎች እንዲሁም ከመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በጠላትነት እንዲሰለፍ በሐሰት ፕሮፖጋንዳ ህዝቡ ተደናግሮና ተገዶ ወደ አስከፊ ጥፋት እንዲገባ መደረጉም በመግለጫው ተመላክቷል፡፡
ስለሆነም የትግራይ ወጣቶች እና ሚሊሻ አባላት በወንጀለኛ መሪዎች ተደናግረው አላስፈላጊ መስዋዕትነት ከመክፈል በመቆጠብ ለመንግስት በሰላም እጃቸውን እንዲሰጡ ሰራዊቱ ጥሪ አቅርቧል ፡፡
ተገደው ወደ ጦርነት የገቡ ወጣቶች እና የሚሊሻ አባላት እጃቸውን ለመንግስት የሚሰጡ ከሆነም ለህይወታቸው ዋስትና እንደሚሰጣቸው ነው ያስታወቀው፡፡
ሠራዊቱ ይህንን ጥሪ ያቀረበውም ካለው ህዝባዊ ባህሪና ለትግራይ ህዝብም ካለው ወገናዊነት መሆኑን አውስቷል፡፡
የሽብር ቡድኑ በፈፀመው ግፍ፣ ባካሄደው ዘረፋ እና ከአብራኩ በወጣው ሠራዊት ላይ የግፍ ጥቃት በፈጸመው ጥቃት የኢትዮጵያ ህዝብ ከዳር እስከዳር ሊፋለመው ቆርጦ መነሳቱን መግለጫው አትቷል፡፡
የሠራዊቱ ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፦
የአሸባሪው ጁንታ ጥቂት መሪዎች ባላቸው ስግብግብ የሥልጣን ፍላጎት እና ከሕግ ተጠያቂነት ለመዳን ሲሉ የትግራይን ሕዝብ ለጦርነት በመማገድ ከንቱ መሥዋዕትነት እያስከፈሉት ይገኛሉ።
ከአጎራባች ክልሎች እና በአጠቃላይ ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋርም በጠላትነት እንዲሰለፍ በሐሰት ፕሮፓጋንዳ ሕዝቡን አደናግረው እና አስገድደው ወደ አስከፊ ጥፋት እየከቱት ነው።
ይህ የጁንታው የጥፋት መንገድ በእጅጉ ያሳሰበው እና የትግራይ ሕዝብን እንደሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ የሚመለከተው የሀገር መከላከያ ሠራዊት በሆደ ሰፊነት ለትግራይ ሕዝብ በተለይም ወጣቶች እና ሚሊሻ አባላት የሚከተለውን ጥሪ አስተላልፏል።
ዕድሜ ዘመኑን “ሥልጣንን ዘላለማዊ ርስቴ ካላደረግኩ ኢትዮጵያን አፈርሳለሁ፤ አሊያም አጥፍቼ እጠፋለሁ” የሚል አስተሳሰብ የተጠናወተው ጁንታ፤ ለሕዝብ እልቂት እና እንግልት ደንታ ስሌለለው ትግራይ ክልል ከገባ ማግስት ጀምሮ ከፌዴራል መንግሥት ጋር ያልተገቡ እሰጥ-አገባዎችን ከመፍጠር ጎን ለጎን በከፍተኛ ቁጥር ልዩ ኃይል እና ሚሊሻ ሲያሰለጥን እና ወደ መንግሥታዊ ሥልጣኑ በኃይል ለመመለስ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ ሀገር የማፍረስ ተግባሩን የትግራይ ሕዝብን ለዓመታት ሲያገለግል የቆየውን የሰሜን ዕዝን ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ ከጀርባ ማጥቃት ጀመረ።
የህወሓት የሽብር ቡድን ኢትዮጵያን በመራባቸው ከሩብ ክፍለ ዘመን በላይ በሆነው የሥልጣን ጊዜው በኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ላይ ለመስማት እጅግ የሚሰቀጥጡ እና ለማመን የሚያዳግቱ ዘግናኝ ግፎችን ፈፅሟል።
ይህንንም በእስር ቤቶች በማጎር፣ ቶርች በማድረግ፣ ጥፍር በመንቀል፣ በማኮላሸት፣ ከአደገኛ አውሬዎች ጋር በማሰር እና በማስበላት መንግሥታዊ ሽብርተኝነት የፈፀመ መሆኑን መላው ሕዝብ እና የጥቃቱ ሰለባዎች የመሰከሩት ሐቅ ነው።
የሽብር ቡድኑ የወንጀሎች ቁንጮ አመራሮች በትግራይ ሕዝብ በተቋቋሙ የተራድዖ ድርጅቶች ስም የቤተሰብ ኔትወርክ በመዘርጋት የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሶችን እና ሕዝቦችን ሀብት ዘርፈው በልጽገውበታል፤ የትግራይ ሕዝብ ከግማሽ በላዩ በምግብ ለሥራ መርሐ-ግብር ኑሮውን እየገፋ እነርሱ ግን ቤተሰቦቻቸውን በአውሮፓ እና በአሜሪካ የቅንጦት ቤት እና መኪና ገዝተው የተንደላቀቀ ሕይወት እንዲመሩ ሲያደርጉ ቆይተዋል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ የጁንታውን ወንጀለኞች ከዳር እስከ ዳር የጠላቸው እና ሊፋለማቸው ቆርጦ የተነሣው በፈፀሙበት ግፍ፣ ባካሄዱበት ዘረፋ ከአብራኩ በወጣው ሠራዊት ላይ የግፍ ጥቃት ስለፈፀሙ እና “ኢትዮጵያን እናፈርሳለን” ብለው በአደባባይ ስለፎከሩ ነው።
እናንተም ለሚያደርጉት እኩይ ተግባራቸው ተባባሪ አትሁኑ። ዓላማቸው እንድትሞቱላቸው በሐሰት ፕሮፓጋንዳ ቀስቅሰው በማሰለፍ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወንድሞቻችሁ ጋር በጠላትነት እንድትፋለሙ እና ትርጉም የሌለው መሥዋዕትነት እንድትከፍሉ ማድረግ ነው።ስትሞቱ እና አካላችሁ ሲጎድል ወላጆቻችሁ ወይም ሚስት እና ልጆቻችሁ ጡረታ ወይም የደም ካሣ አያገኙም። ደማችሁ ደመ-ከልብ ይሆናል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር ሙሉ ድጋፉን የሰጣቸው የሀገር መከላከያ ሠራዊት አባላት፣ የየክልሉ ልዩ ኃይሎች እና ሚሊሻዎች አንድነታቸውን አጠናክረው እያደረጉት ያለውን ሀገራቸውን ከመፍረስ የመታደግ ውጊያ በአሸናፊነት መወጣታቸው እይቀርም።
የአሸባሪው ህወሓት ጁንታዎችም በቅርቡ ለሽንፈት ይዳረጋሉ። ታዲያ ለምን በሽንፈት መደምደሙ ለማይቀር ከንቱ ዓላማ ሕይወታችሁን እና አካላችሁን ትከፍላላችሁ? ቤተሰቦቻችሁንም ለምን ያለረዳት ታስቀራላችሁ? በአሁኑ ሰዓት እናንተን ወደ ጦር ሜዳ የሚማግዱ የሕወሓት አመራሮች ወንጀለኞቹ ጥቂት ሲሆኑ፣ ሕዝቡን ሞቢላይዝ በማድረግ የተሰለፋችሁ ሁሉ ወንጀለኞች ናቸሁ ተብሎ አይታሰብም።
የጁንታው መሪዎች እነርሱ በወንጀለኝነታቸው ለሕግ እንዳይቀርቡ ትታዳጓቸው ዘንድ የትግራይን ወጣቶች፣ ሚሊሻዎች፣ ወንድ እና ሴት ሕፃናትን ያለበቂ ሥልጠና ወደ ጦርነት ይልኳቸዋል። ይህ ድርጊታቸው ትግራይን ያለወጣት፣ አረጋውያንን ያለ ጧሪ የሚያስቀር የጭካኔ ድርጊት ነው።
የፌደራል መንግሥት ለትግራይ ሕዝብ ክብር ሲል የተናጠል ተኩስ አቁም ቢያደርግም ጁንታው ግን “ኢትዮጵያን ሳላፈርስ ውጊያ አላቆምም” ብሎ በጦርነቱ ገፍቶበታል። ጎረቤት ክልሎችንም በመውረር ያሰማራቸውን በርካታ የትግራይ ልጆች ለሞት እና ለአካል ጉዳት ዳርጓል።ሕይወታቸውን ለማዳን ወደ ኋላ በሚሄዱት ላይም በማሰር እና በመረሸን የጭካኔ እርምጃ እንደሚወስድባቸው ከራስህ በላይ ማስረጃ የለም።
ርኅራሔ ያልፈጠረባቸው የጁንታው መሪዎች በጦር ሜዳ የቆሰሉ እና መንቀሳቀስ የማይችሉትን ወንድሞቻችሁን ከውጊያ አፈግፍጋችኋል በማለት ከፊታችሁ ሲረሽኑ እንደነበር ከእናንተ በላይ አስረጂ የለም።ጁንታው በርካቶችን ለከንቱ ዓላማ ለሚያካሂደው ጦርነት ገብሮ እና ወላጆችን የወላድ መኻን አድርጎ አሁንም ተጨማሪ የግድጅ ምልመላዎችን እያካሄደ ነው።
እታገልለታለሁ ለሚለው ሕዝብም ቅንጣት ርኅራሔ የሌለው የጁንታው ወንጀለኛ ስብስብ “በሕዝብ ማዕበል ጦርነትን አሸንፌ ዕድሜዬን አራዝማለሁ” በሚል ኃላፊነት የጎደለው ራስ ወዳድ ውሳኔ ዕድሜ እና ፆታ ሳይለይ ከሕፃን እስከ አዛውንት በጦርነት በመማገድ ለአስከፊ እልቂት እየዳረገ ይገኛል።
አሁንም በርካቶችን ለአላስፈላጊ መሥዋዕትነት ከዳረገ በኋላ “ልጅህን ለዘመቻ የማትልክ ከሆነ ዕርዳታ አይሰጥህም” በማለት ሕዝቡን እያሰቃየው መሆኑ በገሃድ የምታየው እውነት ነው። ስለሆነም የትግራይ ወጣቶች እና ሚሊሻዎች ሆይ፣ ዓላማ ለሌለው ጦርነት መሥዋዕት መሆናችሁ ይብቃ!
በሽንፈት መደምደሙ ለማይቀር ጁንታ መራሹ ጦርነት በከንቱ ማለቃችሁን ለማቆም ቆም ብላችሁ አስቡ። በየግንባሩ ለሚገኘው የሀገር መከላከያ ሠራዊት እጃችሁን በሰላም ብትሰጡ ሠራዊቱ ተቀብሎ በእንክብካቤ እንደሚይዛችሁ፣ ከቆሰላችሁም እንደሚያሳክማችሁ እና ከቤተሰቦቻችሁ ጋር ሰላማዊ ሕይወት እንድትመሩ እንደሚመቻችላችሁ ልንገልጽላችሁ እንወዳለን።
የሀገር መከላከያ ሠራዊት ይህንን ጥሪ የሚያቀርበው ካለው ሕዝባዊ ባህሪ እና ለትግራይ ሕዝብም ካለው ወገናዊነት መሆኑን እየገለጸ፣ እጃችሁን ለመከላከያ ሠራዊት ብትሰጡ ለሕይወታችሁ ዋስትና እንደሚሰጣችሁ በማስገንዘብ ዕድሉን ትጠቀሙ ዘንድ ወገናዊ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
ኢትዮጵያ በልጆቿ አኩሪ መሥዋዕትነት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኖራለች!
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.