Fana: At a Speed of Life!

ሶቦና ሪል ስቴት እና ኮንስትራክሽን አክሲዮን ማህበር 4 ነጥብ 2 ሚሊየን ብር የሚገመት ድጋፍ አደረገ

አዲስ አበባ፣ ህዳር 21፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ሶቦና ሪል ስቴት እና ኮንስትራክሽን አክሲዮን ማህበር 4 ነጥብ 2 ሚሊየን ብር ግምት ያላቸው 100 ሰንጋዎችን እና 150 በግ እና ፍየል ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ድጋፍ አደረገ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ አክሲዮን ማህበሩ ለሰራዊቱ ያደረገውን ድጋፍ በሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የቅርስ ጥበቃና ሙዚየም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄሜራል ደሳለኝ ደቼ አስረክበዋል፡፡
በዚህ ወቅት ወይዘሮ አዳነች ህብረተሰቡ ለሰራዊቱ እያደረገ ያለው የሞራል፣ የገንዘብ እና የቁሳቁስ ድጋፍ ሰላም እንዲሰፍን እና የህግ የበላይነት እንዲከበር ምን ያክል ፍላጎት እንዳለው የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የከተማዋ ነዋሪዎች ሰራዊቱ በጁንታው የህወሓት የጥፋት ቡድን ላይ እርምጃ መውሰድ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ህዝቡ እያደረገ ያለው ድጋፍ አበረታች መሆኑን ገልጸው ከድል በኋላም ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የሶቦና ሪል ስቴት እና ኮንስትራክሽን አክሲዮን ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ቶፊቅ ከድር በበኩላቸው ከአክሲዮን ማህበሩ በጀት እና ከማህበሩ አባላት መዋጮ ከ 4 ነጥብ 2 ሚሊየን ብር በላይ ግምት ያላቸው 100 ሰንጋዎችን እና 150 በግ እና ፍየሎችን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
በቀጣይም ለሰራዊቱም ይሁን አስፈላጊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ድጋፋቸውን ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
በሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የቅርስ ጥበቃና ሙዚየም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ብርጋዴር ጄኔራል ደሳለኝ ደቼ በርክክቡ ወቅት ህብረተሰቡ ላሳየው የሞራል ስንቅ፣ የገንዘብ እና የቁሳቁስ ድጋፍ ምስጋና ማቅረባቸውን ከአዲስ አበባ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.