Fana: At a Speed of Life!

በህወኃት ውስጥ ያለ ቡድን በሰሜን ዕዝ የመከላከያ ሰራዊታችን ላይ ያደረሰውን ጥቃት በእጅጉ ያወግዛል-የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር

አዲስ አበባ ፣ጥቅምት 25 ፣2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ)የድሬዳዋ አስተዳደርና ህዝብ በህወኃት ውስጥ ያለ ቡድን በሰሜን ዕዝ የመከላከያ ሰራዊታችን ላይ ያደረሰውን ጥቃት በእጅጉ እንደሚያወግዝ አስታውቋል።

ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በወቅታዊ ጉዳይ ላይ የሰጠው መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል

የድሬዳዋ አስተዳደርና ህዝብ በህወሃት አገር አጥፊ ቡድን ላይ በሚወሰደው እርምጃ ከፌዴራል መንግስት ጎን ይቆማል ።

የድሬዳዋ አስተዳደርና ህዝብ ሀገርን ከመበተንና የዜጎችን ደህንነት ለማረጋገጥ በህወሃት አጥፊ ቡድን ላይ የመከላከያ ሰራዊታችን በሚወስዳቸው ማንኛውም አይነት እርምጃዎች የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ይገልፃል ፡፡

በሀገራችን እዚህም እዚያም የሚፈጠሩ ዘር ተኮር ጥቃቶች ምንጭ የሆነው ህወሃት በዚህ ሳያበቃ በመከላከያ ኃይላችን የፈጸመው ጥቃት ታሪክ የማይዘነጋውና የቅጥረኝነት ተልዕኮውን የተወጣበት መሆኑ ይታመናል ፡፡

ህወሃት በቀጣይም ኢትዮጵያን ለማተራመስ እያደረገ ያለውን የመጨረሻ መንፈራገጥ እንዳይሳካና ኢትዮጵያውያን ወደጀመሩት ልማት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲመለሱ መከላከያው እየወሰደ ያለውን እርምጃ የድሬዳዋ አስተዳደርና ህዝብ እስከመጨረሻው እንደሚደግፍ እያስታወቀ ሰራዊታችን ለሚወስደው ማንኛውም እርምጃ የድሬዳዋ አስተዳደርና ነዋሪው እስከ ህይወት መስዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን ያረጋግጣል፡፡

የፌደራል መንግስት የሚያወጣቸውን መመርያዎች በሙሉ አቅሙ ለመተግበር ዝግጁ መሆኑን ያሳውቃል ፡፡

የድሬዳዋ አስተዳደር ህዝብ ከጸጥታ አካል ጋር በመሆን በየአካባቢው ጥቃቶች እንዳይፈጠሩ አካባቢያቸውን በንቃት በመጠበቅና ከጸጥታ አካላት ጋር በጋራ በመስራት የበኩላቸውን ሀላፊነት እንድትወጡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.