Fana: At a Speed of Life!

በምርጫ የሕግ ማዕቀፎች ዙሪያ ለፌደራል እና ክልል የፍትሕ ተቋማት ባለሙያዎች ሥልጠና እየተሰጠ ነው

አዲስ አበባ ፣ ጥር 7 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በምርጫ የሕግ ማዕቀፎች ዙሪያ ለፌደራል እና ክልል የፍትሕ ተቋማት ባለሙያዎች እና አመራሮች ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑን ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ አስታወቀ።

በዚህ ሥልጠና ላይ በዋናነት በምርጫ ወቅት በወንጀል የሚያስጠይቁ ተግባራት እና የምርመራ እንዲሁም አጥፊን በሕግ እንዲጠየቅ የማድረግ ሂደትን በተመለከተ የዐቃቤ ሕግ፣ የፓሊስ ተቋማት አመራሮች እና ባለሙያዎች ሚና ይዳሰሳል።

ሥልጠናውን በንግግር የከፈቱት የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ አቶ ፈቃዱ ፀጋ፥ ዜጎች ዴሞክራሲን ከሚለማመዱባቸው መንገዶች አንዱ እና ዋነኛው ምርጫ መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህ ተግባር አደጉ በተባሉ ሀገራት ውስጥ ክርክር ማስነሳቱ በተለያዩ ጊዜያት የሚስተዋል ተግባር መሆኑን አስታውሰዋል።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ የሚካሄደው ምርጫ በሰላም እንዲከናወን እና በምርጫ ሂደት የሚፈፀሙ ወንጀሎች ካጋጠሙም በአግባቡ መመርመር ያስችል ዘንድ የሕግ ማዕቀፎች ላይ ሥልጠና መስጠት አስፈላጊ በመሆኑ ሥልጠናው መዘጋጀቱን ተናግረዋል።

ሠልጣኞች በትኩረት ሥልጠናውን ተከታትለው ወደመጡበት ተቋማት ሲመለሱ ያገኙትን እውቀት ለባልደረቦቻቸው በአግባቡ ተደራሽ እንደሚያደርጉ እምነታቸው መሆኑን ገልጸዋል።

ሥልጠናው በዛሬው ውሎው ስለ ምርጫ በሚደነግገው አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ውስጥ የተካተቱ ዋና ዋና ጉዳዮች የመጀመሪያ ክፍል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሕግ ትምህርት ክፍል መምህር ዶክተር ሲሳይ አልማው ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።

በነገው ዕለትም ሥልጠናው ቀጥሎ ከምርጫ ጋር በተገናኘ በወንጀል የሚያስጠይቁ ተግባራትን እና የምርመራ ጥፋተኛነትን በተመለከተ በተቋሙ ዐቃቤ ሕግ አቶ ሀብታሙ ብርሌ አማካኝነት ሥልጠና የሚሰጥ ይሆናል።

ሥልጠናው እየተሰጠ ያለው ዘንድሮ የሚካሄደውን ስድስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ነፃ እና ፍትሐዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የፍትሕ ተቋማት የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ በመሆኑ እንደሆነም ተገልጿል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.