Fana: At a Speed of Life!

በሶማሌ ክልል የመሰረት ልማት ግንባታዎች በተያዘላቸው የጊዜ ግደብ ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲውሉ አቅጣጫና መመሪያ ተሰጠ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 27፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በሶማሌ ክልል የመሰረት ልማት ግንባታዎች በተያዘላቸው የጊዜ ግደብ በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲውሉ አቅጣጫና መመሪያ ተሰጠ።

የሶማሌ ክልል ለበርካታ ዓመታት ተደራርቦ የቆዩትን የዜጎች የሰላም፣ የመሰረተ ልማት፣ መልካም አስተዳደር፣ ዴሞክራሲ፣ የፍትህና ሰብዓዊ መብት ጥያቄዎችን በአግባቡ ለመመለስ በርካታ ጥረቶች ሲያደርግ መቆየቱን ገልጿል።

እንዲሁም በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ማከናወን እና በተያዘላቸው የጊዜ ገደብና በታቀደላቸው ጥራት ለማጠናቀቅ አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል ሲደረግ መቆየቱንም አስታውሷል።

ከዚህ ጋር ተያይዞም የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጄክቶችን በመጎበኘት ከተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ጋር በማስተያየትና በመገምገም የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አስቀምጠዋል።

ባለፉት ሁለት አመታት ግንባታቸው ሲከናወን የነበሩ ፕሮጀክቶች ስራ እንዲጀምሩ የተደረገ ሲሆን፥ በተለያየ ምክንያት ግንባታቸው የተጓተቱ ፕሮጀክቶችን አመራሩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት አቅጣጫዎችን አስቀምጠዋል።

በዚህም ውል ፈጽመው ስራ ላይ የሚገኙ አንዳንድ የተቋራጭ ድርጅቶች ፕሮጀክቶችን በጊዜ ያለመጨረስ፣ ማጓተትና ተጨማሪ ጊዜ መውሰድ የመሳሰሉ ሰፊ ክፍተት እንዳለባቸው በመስክ ምልከታው ተገልጿል።

በመሆኑም በስራዎች ላይ ለታዩ ክፍተቶች የተቋራጭ ድርጅቶቹ ተጠያቂ መሆናቸውን ያስቀመጠ ሲሆን በአጭር ጊዜ የማስተካከያ እርምጃ ካልወሰዱ አስተዳደራዊ የእርምት እንዲወሰድ ውሳኔ ተላልፏል።

በየዘርፉ ያሉ የክልሉ የስራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎችም በክልሉ እየተሰሩ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ተከታታይና ቀጣይነት ያለው ክትትል እንዲያደርጉ እንዲሁም የእርምት እርምጃዎችን እንዲወስዱ ውሳኔ ላይ መደረሱን ከክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.