Fana: At a Speed of Life!

በተያዘው የመስከረም ወር ስድስት የድንበር ኬላዎች ይከፈታሉ – የኢሚግሬሽን ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 11፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያ ስድስት የድንበር ኬላዎችን እስከተያዘው ወር መጨረሻ ድረስ እንደምትከፍት የኢሚግሬሽን ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ አስታወቀ።

የሚከፈቱት ስድስቱ የድንበር ኬላዎች በቤንሻንጉል፣ በጋምቤላ፣ በሶማሌ እና በደቡብ ክልሎች መሆናቸውንም የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ታምሩ ኡበቱ ገልጸዋል፡፡

ምክትል ዋና ዳይሬክተርሩ ኢትዮጵያ ካላት የድንበር ስፋት አንጻር አሁን ያሏትን 12 የድንበር ኬላዎች ቁጥር መጨመር አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በተለይም የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ ከተለያዩ የውጭ አገራት ድንበሮችን አቋርጠው በህገ-ወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡትን ለመቆጣጠር የድንበር ኬላዎች እንዲከፈቱ አቅጣጫ መቀመጡን አስታውሰዋል።

በመሆኑም ኤጀንሲው ከክልሎች ጋር በመሆን የድንበር ኬላዎችን በጥናት ለመክፈት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።

በጥናት ከተለዩ የድንበር ኬላዎች ውስጥ ስድስቱ እስከዚህ ወር መጨረሻ ድረስ ሙሉ ለሙሉ ክፍት ይሆናሉ ብለዋል፡፡

እንዲሁም ካላቸው ጠቀሜታ አንጻር አንዳንዶቹ በይፋ ባይመረቁም በአሁኑ ወቅት ሥራ እንዲጀምሩ መደረጉን ተናግረዋል።

ኬላዎቹ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው አገልግሎት እንዲሰጡ መሰረተ ልማት የማሟላት ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አንስተዋል።

በኮቪድ -19 ምክንያት በህገ-ወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ሰዎችን ለመቆጣጠር ሲባል ኬላዎቹ በይፋ እስኪከፈቱ ድረስ የተወሰኑት የሰው ኃይል ተመድቦላቸው አገልግሎት መስጠት እንደጀመሩም አቶ ታምሩ ተናግረዋል።

ለኬላዎቹ አስፈላጊውን መሰረተ ልማት በማሟላት እስከ መስከረም 30 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ስድስቱም ኬላዎች ሙሉ ለሙሉ ሥራ እንደሚጀምሩ አስታውቀዋል።

ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ድንበሮች መከፈታቸው በህገ-ወጥ መንገድ ወደ አገር የሚገቡ ሰዎችን በመቆጣጠር የአገርን ደህንነት ለመጠበቅ ያስችላል ብለዋል፡፡

በተጨማሪም ድንበር በሚጋሩ በሁለት አገራት መካከል የዲፕሎማሲና ሌሎች ግንኙነቶች እንዲጠናከር በማድረግ በኩል አስተዋጽዖ ይኖረዋል ሲሉ ተናግረዋል።

በመጨረሻም ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ  ድንበሮች ሲከፈቱ የንግድ ልውውጥና የምጣኔ ሃብት እንቅስቃሴዎች እንደሚጠናከሩ መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.