Fana: At a Speed of Life!

በአቶ ደጀኔ ጣፋ፣ አቶ መስተዋርድ ተማምና በአቶ ጃዋር መሀመድ የኮምፒውተር ባለሙያ ላይ ክስ ተመሰረተ

አዲስ አበባ ፣ ነሀሴ 27 ፣2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኦፌኮ የቀድሞ አመራረ አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ አቶ መስተዋርድ ተማም እና የአቶ ጃዋር መሀመድ የኮምፒውተር ኢንጂነሪንግ ባለሙያ አቶ ሚሻ አደም ላይ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክስ ተመሰረተ።

ክሱ በሁለት የተከፈለ ሲሆን፥ 1ኛ ተከሳሽ አቶ ደጀኔ ጣፋ እና አቶ መስተዋርድ ተማም ላይ ሲሆን፥ ሁለተኛው በአቶ ሚሻ አደም ላይ ነው ።

የአቃቤ ህግ ክስ እንደሚያመለክተው በ1996 ዓመተ ምህረት የወጣውን የኢፌዴሪ የወንጀል ህግ 238/2 ስር የተመለከተውን በመተላለፍ ካልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው ጋር በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በሀይል፣ በዛቻ እና ህግወጥ በሆነ በማንኛውም መንገድ በህግመንግስት የተቋቋመን ስርዓት ለማፍረስ በማሰብ ”ከሰኔ 2012 ዓመተ ምህረት በኋላ የመንግስት የስልጣን ዘመኑ የሚያበቃ በመሆኑ መንግስት ሆኖ መቀጠል ስለማይችል‘ በማለት የሽግግር መንግስት እንዲቋቋም ግፊት ሲያደርጉ እንደነበር አቃቤ ህግ በክሱ ጠቅሷል።

”በሀገሪቱ የሚገኙ የሚኒሊክና ተመሳሳይ ሀውልቶች መፍረስ አለባቸው፣ የኦሮሞ ቄሮዎች የሌሎች ብሄሮችን ንብረት ማቃጠል አለባቸው‘ በሚል በሰኔ 23 ቀን 2012 ዓመተ ምህረት የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ አስቀድመው የሰጡትን እና በተመሳሳይ መዝገብ ተጠርጣሪ የሆኑት አቶ ጃዋር መሀመድ ከጥዋቱ 1 ሰዓት ሲሆን፥ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ ስምንት ጳውሎስ ሆስፒታል አካባቢ የሟች አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ አስክሬንን ለመሸኘት ለተሰበሰበ በርካታ ህዝብ ”ከአሁን በኋላ ብቻችንን አናለቅስም፣ የነፍጠኛ ልጆች ከዚህ በፊት እንደጨረሱን ሁሉ አሁንም እየጨረሱን ነው፣ አሁኑኑ ወደ ሚኒሊክ ሃውልት ሂዱና አፍርሱ፣ አንድ ነፍጠኛ ከመጣ እንዳታልፉት እርምጃ ውሰዱባቸው፣ ከዚያ ወደ አራት ኪሎ ቤተ መንግስት በመሄድ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ያለውን ስርዓት መገርሰስ አለብን‘ በማለት የተሰጣቸውን ተልዕኮ ለማሳካት አንደኛ ተከሳሽ አቶ ደጀኔ ጣፋ በተመሳሳይ መዝገብ ተጠርጣሪ ከሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ጋር ወጣቶችን በማደራጀት ቡራዩ ከተማ ኬላ አስክሬኑ እንዳያልፍና ”አስክሬኑን ወደ አዲስ አበባ እንዲመለስ ማድረግ አለብን‘ የሚል ትእዛዝ በስልክ ተቀብሎ በዚሁ ስፍራ ከግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን መሳሪያ የያዙ በርካታ ወጣቶችን በማስተባበር መንገድ በመዝጋት አስክሬኑን ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸው በክሱ ተመልክቷል።

በሰኔ 22 ቀን ደግሞ ከሌሊቱ 5 ሰዓት ከ10 ላይ በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን ደምበል በተባለ ቦታ ካልተያዘ ግብረ አበሩ ጋር መንገድ እንዲዘጋ በማድረግ መንግስትን ከስልጣን ለማስወገድ የመጨረሻ ትግል እንዲያደርጉ አቶ ደጀኔ ትእዛዝ መስጠታቸው በክሱ ተጠቅሷል።

በሰኔ 23 በምእራብ ወለጋ ነጆ ወረዳ ያልተያዘ ግብረ አበሩ የየአካባቢውን የመንግስት መዋቅር እንዲያፈርሱ ትእዛዝ ያስተላለፉ መሆኑንም ነው ያመለከተው።

ሁለተኛ ተከሳሽ መስተዋርድ ተማም ደግሞ ከጃዋር መሀመድ የተሰጠውን ተልዕኮ ተቀብሎ ቡራዩ ከተማ ኬላ ላይ አስገድዶ አስክሬኑን ወደ አዲስ አበባ በመመለስ የኦሮሞ የባህል ማዕከል መግቢያ በር ጥሶ ሲገባ መያዙን የጠቀሰው በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የደምበል አስተዳደር ፅህፈት ቤት እና የማህበረሰብ ፖሊስ ቢሮን በአጠቃላይ ግምታቸው ከ700 ሺህ ብር የሚበልጥ ንብረት በማውደም እንዲሁም የግል ምግብ ቤትና የመጠጥ ንግድ ተቋማት ላይ ከ824 ሺህ ብር በላይ የሚያወጣ ንብረት የአምስት ግለሰቦች ምግብ ቤትና የዘይት ማምረቻ ፋብሪካን ጨምሮ 3 ነጥብ 7 ሚሊየን ብር የሚያወጣ ንብረት የተቃጠለ መሆኑን እና 5 ሚሊየን ብር የሚያወጡ ተሽከርካሪዎች የተቃጠሉ መሆናቸውን የጠቀሰው አቃቤ ህግ በዚህ ወንጀል ተግባር ምክንያት በተነሳ ግጭት በቡራዩ የሁለት ሰዎች እና በአዲስ አበባ የስድስት ሰዎች ህይወት ያለፈና በህዝብ ደህንነት ወይም ኑሮ ላይ ከፍተኛ ቀውስ የደረሰ በመሆኑ ተከሳሾች በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በህግመንግስቱና በህግመንግስታዊ ስርዓቱ ላይ የሚፈፀም ወንጀል ክስ ቀርቦባቸዋል።

ተከሳሾቹ ክሱ የደረሳቸው ሲሆን፥ ክሱን ተመልክቶ ለመከራከርና ዋስትና እንዲፈቀድላቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል።

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ የፀረ ሽብር ጉዳዮች ወንጀል ችሎት የተገኘው አቃቤ ሀግ ክሱ ከ15 ዓመት በላይ የሚያስቀጣ መሆኑን ተከትሎ በስነ ስርዓት ህጉ መሰረት ዋስትና ያስከለክላቸዋል ሲል ተቃውሞ ተከራክሯል።

ጉዳዩን የተከታተለው ፍርድ ቤቱም መርምሮ የዋስትና ክርክሩ ላይ ብይን ለመስጠት ለነገ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

አቶ ሚሻ አደምም በቴሌኮም ማጭበርበር ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል።

የቴሌኮም ማጭበርበር አዋጅ ቁጥር 761/2004 አንቀፅ 9/1 ስር የተመለከተውን በመተላለፍ በግለሰብ እጅ መያዝ የሌለበትና የማይፈቀደውን አቶ ጃዋር መሀመድ ከኢትዮቴሌኮም ፍቃድ ሳይኖራቸው የሳታላይት መሳሪያ ከአሜሪካ ወደ ሀገር ውስጥ በማስገባት በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 ጃፓን ኤምባሲ አካባቢ በአቶ ጃዋር መሀመድ መኖሪያ ቤት በመትከል በሞባይል ስልክ፣ በታብሌትና ኮምፒውተር የረዥም ርቀት ግኑኝነት በማድረግ የግል የዳታ እና የቪዲዮ ከአምሰት እስከ 25 ኪሎ ሜትር ርቀት ሲስተም ውስጥ ያሉ ተጠቃሚዎች የኢንተርኔት አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ፣ በቤታቸው ውስጥ የግል ኔትወርክ ሲስተም እንዲኖር በማድረግ እና የቪዲዮ ዳታ ግኑኝነት እንዲኖር በማድረግ በሀምሌ 4 ቀን 2012 በመኖሪያ ቤታቸው ነቅለው ከደበቁበት በክትትል በቁጥጥር ስር ውሏል ብሏል።

ካለፍቃድ የቴሌኮም መሰረተ ልማት መዘርጋት ወንጀል ክስ ቀርቦበታል።

ተከሳሹ በዋስትና እንዲፈታ የጠየቀ ሲሆን፥ አቃቤ ህግ ክሱ ከ20 ዓመት በላይ የሚያስቀጣ በመሆኑ እንዲሁም ተከሳሹ ከሀገር ሊያመልጥ ሲል በቁጥጥር ስር የዋለ መሆኑን ጠቅሶ ዋስትናን ተቃውሟል።

ክርክሩን የተከታተለው ፍርድ ቤቱ ብይን ለመስጠት ለነገ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

በታሪክ አዱኛ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.