Fana: At a Speed of Life!

በደቡብ ክልል በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ እየቀረበ  ነው -የክልሉ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 4 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ)በደቡብ ክልል በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ እየቀረበ  መሆኑን የክልሉ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡

በደቡብ ክልል በተለያዩ ዞኖች በመሬት ናዳ፣ በጎርፍ፣ በውሃ መጥለቅለቅ፣ በድርቅ፣ በመሬት መሸራተት ፣ በእሳት አደጋ፣ በግጭቶችና በሌሎች ምክንያቶች ለተፈናቀሉ ወገኖች ሰብአዊ ድጋፍ እየቀረበ መሆኑን የክልሉ የአደጋ ስጋር ስራ አመራር ኮሚሽን አስታውቋል፡፡

የኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ጋንታ ጋምኣ ÷በበልግ ወቅት መዛባት ምክንያት ለምግብ ክፍተት ለተጋለጡ ወገኖች 270 ሚሊየን ብር የሚጠጋ ገንዘብ  ከመሰራጨቱም ባለፈ በ37 ወረዳዎች ለሚኖሩ ከ207 ሺህ በላይ ህጻናትና እናቶች ከ10 ሺህ ኩንታል በላይ አልሚ ምግብ ድጋፍ መደረጉን ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም ገለጻ በ2012 የክረምት ወራት በደቡብ ኦሞ ዳሰነች ወረዳ የደረሰውን የኦሞ ወንዝ ሙላት ጉዳትና በተራራማ አካባቢዎች በየዓመቱ የሚከሰቱ የመሬት መንሸራተትና ናዳ ችግሮች እንዲሁም የጎርፍ መጥለቅለቅ በሚበዛባቸው አካባቢዎች ጉዳቱን የሚቀንሱ ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል፡፡

በክልሉ ባለፉት 6 ወራት በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች በ11 ዞኖች በ45 ወረዳዎችና 3 ከተማ አስተዳደሮች  እንዲሁም በ4 ልዩ ወረዳዎች ከ310 ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎች የተፈናቀሉ ሲሆን ከ9 ሺህ በላይ በሚሆኑ ቤቶች ላይ ጉዳት  መድረሱን ተናግረዋል፡፡

የክልሉ መንግስትም  ባለፉት ዓመታት በተለያዩ አካባቢዎች ለተፈናቀሉ ወገኖች ማገገሚያ እና መልሶ ማቋቋም ስራዎች ከ836 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ማድረጉንም ገልፀዋል፡፡

አያይዘውም ለነዚህ የሕብረተሰብ ክፍሎች ምግብና ምግብ ነክ ድጋፎችን ከማድረግ ባለፈ ተፈናቃዮችን መልሶ ለማቋቋምና ለእንስሳት መኖ ለማቅረብ የክልሉ መንግስት   የተቀናጀ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም ችግሩን ለመቅረፍ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና የተባበሩት መንግስታት ተቋማትም ድጋፍ ማድረጋቸውን አቶ ጋንታ ገልጸዋል፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የጤና፣ የመጠጥ ውሃ እና የትምህርት አገልግሎቶችን ተደራሽ ለማድረግ ሲሰራ ቆይቷልም ነው ያሉት፡፡

ኮሚሽኑ ከግጭት ጋር የተያያዙ አደጋዎችን ለመቀነስና በህብረተሰቡ ውስጥ ያሉ ቅሬታዎችን ለመፍታት እንዲሁም ከተፈጥሮ አደጋዎች አኳያ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን ለማሳደግ በልዩ ትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል።

በቀጣይም ማህበረሰቡ ከመንግስት ጎን በመቆም የመልሶ ማቋቋም ስራዎችን እንዲደግፍ ጥሪ ማቅረባቸውን ከክልሉ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.