Fana: At a Speed of Life!

በደገሀቡር እና በጅግጅጋ ሪፈራል ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል ያገባኛል ኢኒሼቲቭ ተጀመረ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 5 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በሶማሌ ክልል በደገሀቡር ሆስፒታል እና በጅግጅጋ ሪፈራል ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል የህክምና አገልግሎት ጥራትን፣ ፍትሀዊነትንና ተደራሽነትን እንደሚያሻሽል የታመነበት ያገባኛል /I CARE/ የተሰኘው ኢኒሼቲቭ በይፋ ተጀምሯል።

በማስጀመሪያ መረሀግብሩ ላይም የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ሳህረላ  አብዱላሂ ተገኝተዋል።

በወቅቱም የጤና ሚኒስቴር በሀገሪቱ የህክምና ተቋማት የህክምና አገልግሎት ላይ የሚያጋጥሙ ችግሮችን ከመሰረቱ ለመፍታት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ወይዘሮ ሳህረላ   ተናግረዋል።

በዚህም  ያገባኛል  የተሰኘው ኢኒሼቲቭ  ጥራትን፣ ፍትሀዊነትን፣ ተደራሽነትን እና ሌሎች በህክምና ተቋማት የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ አንዱ  ኢኒሼቲቭ  መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በመሆኑም በጅግጅጋ  ዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል እና በደገሀቡር ሆስፒታል ጥራትን፣ ፍትሀዊነትን እና ተደራሽነትን ለማምጣት እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን በማገዝ ረገድ ያገባኛል የተሰኘው ኢኒሼቲቭ  በአግባቡ መተግበር ትልቅ ሚና እንደሚኖረው  ገልጸዋል፡፡

ሚኒስትር ዴኤታዋ በደገሀቡር እና በጅግጅጋ ሪፈራል ሆስፒታሎች ተዘዋውረው ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በሆስፒታሎቹ የሚታዩ የህክምና መሳሪያዎች ፣ የደም ባንክ አገልግሎት፣ የመድሀኒት እና መሰል ችግሮችን ለመፍታት ከክልሉ ጤና ቢሮ ጋር በመሆን ሚኒስትር መስሪያቤቱ አስፈላጊውን እገዛ እንደሚያደርግም ነው የገለጹት፡፡

በደገሀቡር ሆስፒታል ለዘመናዊ የፋርማሲ አገልግሎት የተሰራውን ህንጻም መርቀዉ ያስጀመሩ ሲሆን÷ እየተገነቡ ያሉ ማስፋፊያዎች ያሉበትን ደረጃ ተመልክተዋል፡፡

በመርሀግብሩ ላይ የጤና ሚኒስቴር የስራ ሀላፊዎች፣ የሱማሌ ክልል ጤና ቢሮ የስራ ሀላፊዎች፣ የጅግጅጋ ዩኒቨርስቲ የስራ ሃላፊዎች፣ የደም ባንክና የተቋማቱ ሰራተኞች መገኘታቸውን ከጤና ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.