Fana: At a Speed of Life!

በጋምቤላ ክልል ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ ይዘው ለማምለጥ በሞከሩ አዘዋዋሪዎች ላይ እርምጃ ተወሰደ

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 20 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ አዘዋዋሪዎች ከጸጥታ አካላት ለማምለጥ ባደረጉት የተኩስ ልውውጥ እርምጃ እንደተወሰደባቸው የክልሉ ፓሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።

የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ኮማንደር ኡማን ኡጋላ  እንደተናገሩት እርምጃው የተወሰደው ግለሰቦቹ ትናንት ምሽት አራት ስዓት ላይ ከኑዌር ዞን ወደ ኢታንግ ልዩ ወረዳ ጦር መሳሪያዎችን በሸክም ለማስገባት ሲሞከሩ ነው።

እነሱን ለመያዝ በተደረገው የተኩስ ልውውጥም ሁለት ጦር መሳሪያ አዘዋዋሪዎች መሞታቸውንና አንዱ ደግሞ ቆስሎ መያዙን ተናግረዋል።

በግለሰቦቹ እጅ የነበሩት 19 ታጣፊና ዘጠኝ ባለሰደፍ በድምሩ 28 የክላሽንኮቭ ጠመንጃዎች መያዛቸውን ለኢዜአ ገልጸዋል።

ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ አዘዋዋሪዎች በእጃቸው ይዘዋቸው የነበሩትን ሌሎች መሳሪያዎች እየተታኩሱ ይዘው ማምለጣቸውን ጠቁመው “እነሱን ለመያዝ ፖሊስ አስፈላጊውን ክትትል እያደረገ ነው” ብለዋል።

ቆስሎ በቁጥጥር ስር በዋለው ተጠርጣሪ ላይ በተደረገው ማጣራት ባመለጡት ግለሰቦች እጅ 48 የሚሆኑ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያዎች እንደነበሩ ማረጋገጥ መቻሉንም ጠቁመዋል።

በወረዳው የጦር መሳሪያዎችን ይቀበላሉ ተብሎ የተጠረጠሩ ሁለት ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና አስፈላጊው የማጣራት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስታውቀዋል።

በተለይም ክልሉ ከደቡብ ሱዳን ጋር ሰፊ የድንበር ወሰን ያለው ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በርካታ የጦር መሳሪያ በክልሉ በኩል አድርጎ ወደ ተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ይገባል ተብሎ እንደሚገመትም አስረድተዋል።

የጦር መሳሪያዎቹ ለሽብር ወንጀል ካልሆነ በስተቀር ለሌላ ተግባር ስለማይውሉ ዝውውሩን ለመግታት ለሚደረገው ጥረት መሳካት ህብረተሰቡ የጀመረውን ተሳትፎ አጠናክሮ እንዲቀጥል ኮሚሽነሩ ጥሪ አቅርበዋል።

“የኢታንግ ልዩ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ኦኬሎ ኡቦንግ በወረዳው ህዝቡን በማሳታፍ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውሩን ለማግታት እየተሰራ ነው” ብለዋል።

በትላንትናው ዕለት የተወሰደው እርምጃና የተገኘው ውጤት ከህብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማና ትብብር የተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.