Fana: At a Speed of Life!

ቤተመንግስት ቦምብ ለማስወርወር አባላትን ሲመለምሉ  የነበሩ ግለሰቦች ክስ እንዲሻሻል ብይን ተሰጠ

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 4 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በቤተመንግስት ቦምብ ለማስወርወር 1 ሚሊየን ብር ይሰጣችኋል በማለት አባላትን ሲመለምሉ ነበር የተባሉ ሶስት ግለሰቦች ላይ የቀረበው ክስ እንዲሻሻል ብይን ተሰጠ።

ክሱ እንዲሻሻልብይን የሰጠው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 2ኛ የጸረ ሽብርና የህገ መንግስት ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው።

በህዳር ወር 2013 ዓ.ም በአዲስ አበባ ለሽብር መሰናዳት ሙከራ ወንጀል ፈጽመዋል ተብለው ክስ ቀርቦባቸው የነበሩት ተከሳሾች 1ኛ ተከሳሽ አለማየሁ ፈይሳ 2ኛ ጣሂር አደም እና ዳንኤል ሰለሞን ይባላሉ።

በተከሳሾቹ ላይ ቀርቦ የነበረው የዐቃቤ ህግ ክስ እንደሚያመላክተው በ1996  ዓ.ም የወጣውን የወንጀል ህግ አንቀጽ 32  እና በ2012 ዓ.ም የወጣውን የጸረ ሽብር አዋጁን በመተላለፍ ነው።

በዚህም 1ኛ ተከሳሽ አለማየሁ ፈይሳ ከሚኖርበት ነቀምት ወደ አዲስ አባባ በመምጣት በህዳር ወር 2013 ዓ.ም ለአባ ቶርቤና ኦነግ ሸኔ ቡድን ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎችን በመመልመል ጥቃት የሚፈጸምባቸው  የተመረጡ የመንግስት ተቋማትን፣ ሰራተኞችን፣ የተለያዩ ሃይሎችን  የመለየት ስራ መስራቱን በክሱ አመላክቷል።

በተጨማኛሪም ተከሳሹ  በአራት ኪሎ ቤተመንግስት ላይ ቦምብ  የሚወረውሩ አባላትን በመመልመል በአዲስ አባባ ከ30 እስከ 40 የሚደርሱ የኦነግ ሸኔ አባላቶች አሉ ለምን ከእነርሱ ጋር አትሰሩም፤ ይህን ከሃዲ መንግስት ማውረድ አለብን 4 ኪሎ ቤተመንግስት ላይ  ቦምብ በመወርወር ጥቃት ታደርሳላችሁ ለዚሀም  አንድ ሚሊየን ብር ይሰጣችኋል ብሎ ሲሰራ እንደነበርተመላክቷል።

በተጨማሪም ለቦምቡ አወራወር ለሶስት ቀን የቦምብ አወራወር ስልጠና ትወስዳላቸሁ በማለትና በማሳመን ሲሰራ እንደነበር ዐቃቤ ህግ በክሱ ጠቅሷል።

ሌሎችን 2ኛ እና 3ኛ ተከሳሾች ከ1ኛ ተከሳሽ ጋር በመሆን አባላት በመመልመል ተግባር በጋራ ሲሰሩ እንደነበርም በክሱ ተጠቅሷል።

በዚህ መልኩ በቀረበባቸው ክስ ላይ ተከሳሾቹ መቃወሚያ አቅርበዋል።

በመቃወሚያቸውም  እንደጠቀሰው በቡድን ተፈጸመ ተብሎ የቀረበው ክስ የህግ አግባብነት የሌለው ነው ብለዋል።

ተመለመሉ የተባሉት እነማን እንደሆኑና  መቼ  እንደሆነ ያልተገለጸ ነው ሲሉ   ክሱ ውድቅ እንዲደረግላቸው በጽሁፍ ባቀረቡት የክስ መቃወሚያ  ገልጸዋል።

ዐቃቤ ህግም በመጋቢት 30 ቀን 2013 ዓ.ም በጽሁፍ ባቀረበው የክስ መቃወሚያቸው ምላሽ ላይ  ክሱ አግባብነት ያለው መሆኑን በመጥቀስ የአባ ቶርቤና የኦነግ ሸኔ ቡድን ጋር እንደሚሰሩ  አመላክቷል።

በቤተ መንግስት ቦምብ የሚወረውሩ አባላትን ሲመለምሉ መገኘታቸውን ተከትሎ  የወንጀል ህጉን በመተላለፋቸው መከሰሳቸው አግባብነት ያለው መሆኑን በሰጠው ምላሽ  አብራርቷል።

በዚህ መልኩ የክስ መቃወሚያውን እና የዐቃቤ ህግ ምላሸን የመረመረው ችሎቱ  የቀረበው ክስ  የተከሳሾቹን የመከላከል መብት የሚያጣብብ ነው ሲል ተከሳሾቹ ተመለመሉ የተባሉ  አባላት መቼ እደሆነ እነማን እንደሆኑ፣ ለጥቃት ተለዩ የተባሉ የመንግስት ተቋማት እና ሰራተኞች እነማን እንደሆኑ በስም ተጠቅሶ  ክሱ እንዲሻሻል ሲል ፍርድቤቱ ብይን ሰጥቷል።

በታሪክ አዱኛወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.