Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያና አልጄሪያ የንግድ ግንኙነታቸውን ለማሳደግ ተስማሙ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 20፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያና አልጄሪያ የንግድ ግንኙነታቸውን ለማሳደግ ተስማምተዋል።
በአልጄሪያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው እና የአልጄሪያ የንግድ ሚኒስትር ካሚል ረዚግ በዛሬው እለት ኢትዮጵያና አልጄሪያ ያላቸውን የንግድ ግንኙነት ይበልጥ ለማሳደግ ያለመ ውይይት አካሂደዋል።
በዚህም ውይይት አልጄሪያና ኢትዮጵያ ያላቸውን ጠንካራ የፖለቲካ ግንኙነት በንግድ ልውውጥ መስክም ሊደግሙት እንደሚገባ ተስማምተዋል።
ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ በሁለቱም ሃገራት የንግድ ማኀበረሰብ ሙሉ ዝግጁነት እንዳለ መኖሩን ገልፀዋል፡፡
ሁለቱ ሃገራት በአውሮፓውያኑ 2017 የንግድ ስምምነት ያላቸው ቢሆንም በሁለቱ ሃገራት መካከል የንግድ ልውውጡን ለማሳደግ በየጊዜው ተቀራርቦ መስራት እንደሚያስፈልግ አስታውቀዋል፡፡
የአልጄሪያ የንግድ ሚኒስትር ካሚል ረዚግ በበኩላቸው÷ ሁለቱ ሃገራት በአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ተግባራዊ ሲሆን በክፍለ አህጉሩ ንግድ ከፍተኛ ተሳታፊ ሊሆኑ የሚችሉበት ሠፊ ዕድል እንዳለ አመልክተዋል።
የንግድ ልውውጡን ለማጠናከር በሁለቱ ሃገራት መካከል ኢትዮጵያ-አልጄሪያ የንግድ ካውንስል መመስረትና ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
አምባሳደር ነብያት በአልጀርስ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የንግድ ልውውጡን ለማሳደግ ንቁ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን ገልፀው÷በፈረንጆቹ ጃኑዋሪ 18 ቀን 2021 በኤምባሲው በተዘጋጀው የኢትዮጵያ አልጄሪያ የዌቢናር የንግድ ውይይት የአልጄሪያ ኩባንያዎች እንዲሳተፉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
ሚኒስትር ካሚል ረዚግ ወደ ኢትዮጵያ የንግድ ልዑካን ቡድን ይዘው ከመጓዝ አንስቶ ለኢትዮጵያ አልጄሪያ የንግድ ካውንስል ምስረታ አስፈላጊውን ድጋፍና የቅርብ ክትትል እንደሚያደርጉ መግለጻቸውን አልጄሪያ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.