Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ ያለምንም እንቅፋት የሠላም ማስከበር ተልዕኮዋን እየፈጸመች ትገኛለች – ሌተናል ጄነራል ደስታ አብቼ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 2፣ 2013 (ኤፍቢሲ) ኢትዮጵያ የሠላም ማስከበር ተልዕኮዋን እንደወትሮው ያለምንም እንቅፋት በመፈፀም ላይ እንደምትገኝ የመከላከያ ሠላም ማስከበር ማዕከል ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ አስታወቁ።

ሌተናል ጄኔራል ደስታ አንዳንድ የጁንታው ተላላኪዎች የኢትዮጵያ ሠላም አስከባሪ ሠራዊት ተከፋፍሏል በማለት የሚነዙት አሉባልታ መሰረተ ቢስ መሆኑንም ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ በአሚሶም ጥላ ስር በሶማሊያ፣ በሱዳን ዳርፉር፣ በሱዳንና በደቡብ ሱዳን ደግሞ የአቢዬ ጊዜያዊ የጸጥታ ኃይል ‘ዩኒስፋ’ ጥላ ስር ሠላም እያስከበረች ነው።

በደቡብ ሱዳን ጁባ በጥቅሉ 11 ሺህ ገደማ ወታደሮችን በማሰለፍ በቀጣናው የሠላም ማስከበር ስራዋን እያከናወነች መሆኑንም ተገልጿል።

ሌተናል ጄኔራሉ ባለፈው ወር የህወሓት የጥፋት ቡድን በሰሜን ዕዝ ላይ የፈጸመውን ኢ-ሠብዓዊ ተግባርና መንግስት የወሰደውን የሕልውናና የሕግ ማስከበር ዘመቻ በማስታወስ ወቅታዊ ሁኔታውን አብራርተዋል።

የአገር መከላከያ ሠራዊት በአገር ውስጥ የሕግ ማስከበር ዘመቻ መጀመሩን ተከትሎ በውጭ አገር ላሉት ሠላም አስከባሪዎች ስለተፈጠረው ሁኔታ ገለጻ መደረጉንም ገልጸዋል።

በዚህም በሁሉም ቀጣና የሠላም ማስከበር ተግባር ላይ የሚገኙ የሠራዊቱ አባላት ድርጊቱን ማውገዛቸውንና የተወሰደውን ህግ የማስከበር እርምጃ ማድነቃቸውን ተናግረዋል።

ሠራዊቱ ያለምንም እንቅፋት የተለመደ የሠላም ማስከበር ተልዕኮውን መቀጠሉንም በመግለጽ ሌተናል ጄኔራል ደስታ የጁንታው ተላላኪዎች በሠላም አስካባሪው የኢትዮጵያ ሠራዊት መካከል መከፋፈል አለ በሚል የሚነዙት አሉባልታ መሰረተ ቢስ ነው ብለዋል።

ሰሞኑንም በተለያዩ የተልዕኮ ቀጣናዎች የሠላም አስከባሪ ወታደሮች ልውውጥ በተለመደው መልኩ እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል።

የሀገር መከላከያ ሠራዊት በቂ አቅም የፈጠረ በመሆኑ በሀገር ውስጥ የሕግ ማስከበር ዘመቻ ምክንያት በሠላም ማስከበር ላይ የሚገኝ ሠራዊት ወደ ሀገር አለመጠራቱንም አክለዋል።

እንደ ኃላፊው ገለጻ የኢትዮጵያ ምልክት የሆነው የሠላም ማስከበር ተልዕኮ ወደፊትም በተሻለ መልኩ ይቀጥላል ብለዋል።

የአሀገር መከላከያ ሠራዊቱ ከራሱ ይልቅ ለሀገርና ለሕዝብ ቅድሚያ ሰጥቶ መስዋዕት የሚሆን “የኢትዮጵያ ሠራዊት” እንጂ የፓርቲ ወይንም የግለሰብ አለመሆኑንም ሌተናል ጄኔራል ደስታ ተናግረዋል።

በሁሉም ግዳጅ ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሠላም አስከባሪ ሠራዊት እንደወትሮው ሁሉ ተልዕኮውን አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪ ማቅረባቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.